Wednesday, 25 July 2018

የጽድቅ ልብስ



ለሰው ልጅ እጅግ በጣም አስፈላጊ ከሚባሉት ጉዳዮች መካከል ልብስና መጠለያ ናቸው። እኛም እነዚህን ነገሮች  ከገሀዱ ዓለም ራሳችንን የምንሸፍንበት ዋንኛ መጠቀሚዎቻችን ናቸው። ሰዎች ሁላችንም ስንባል ሳንሸፈን መኖር አንችልም። በህይወት ዘመናችን በሙሉ በሚያስብል ሁኔታ በሚሸፍነን ውስጥ ተከልለን የምንኖር ጥገኞች ነን።

የመጀመሪያዎቹ ፍጥረታት የሆኑትን አዳምና ሔዋንን ብንመለከት በኋጢአት ከወደቁ በኋላ ክፉንና ደጉን በመለየታቸው ራሳቸውን የሚሸፍን የኮባ ቅጠል እንደለበሱና ነገር ግን እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሚያስፈልገውን የሚያውቅ ቸር ነውና ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስን በጥላነት የሚያሳየውን የበግ ቁርበት አድርጎላቸው በሚበልጠው እንዳለበሳቸውና እንደሸፈናቸው መፅሐፍ ቅዱስ ይናገራል።

በብሉይ ኪዳን የሰውን በደል መርምሮ በማወቅ የሚታወቀው የዳዊት ልጅ ጠቢቡ ሰለሞን ነው።  ስለ ሰለሞን ሁላችንም ከልጅነታችን ጀምሮ የምናውቀው በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተፃፈ አንድ ታሪክ አለ። (1ኛ ነገ 3፥16-28) ሰለሞን እንዴት አድርጎ ሁለቱን ሴቶች እንደመረመረና ሐሰተኛዋን ከእውነተኛይቱ እንደለየና እውነቱን እንዳጋለጠ ብሎም ጉዳዩንም እስራኤል ሁሉ እንደሰሙ ይታወቃል።

አብዛኞቻችን ማጋለጥ ብቻ እውነት የሚመሰለን እንኖር ይሆናል ነገር ግን መሸፈንም እውነት ነው። መፅሐፍ እንዲህ ይላል

የእግዚአብሔር ክብር ነገርን መሰወር ነው፤ የነገሥታት ክብር ግን ነገርን መመርመር ነው።
                                                         ምሳ 25፥2

እግዚአብሔር ሸፋኝ አምላክ ነው። የአደባባይ ነውራችንን በመሸፈን በጉዋዳ የሚገስፅ መልካም አባት። እግዚአብሔር የእኛ ነውር በአደባባይ እንዲጋለጥ አይወድም ለዚህም እኛ ከሰዎች ጋር እርስ በእርስ ባለን ግንኙነቶች ችግር እንኳ ቢፈጠር እንደ ማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 18፥15 መሰረት ወንድምህ ቢበድልህ በመጀመሪያ ብቻህን ውቀሰው ይላል። ይህ የሚያሳየው ምን ያህል እግዚአብሔር ነውራችንን ለመሸፈን እንደሚፈልግ ነው። በሌላ በኩል ወንድሞች ሆይ፥ ሰው በማናቸውም በደል ስንኳ ቢገኝ፥ መንፈሳውያን የሆናችሁ እናንተ እንደዚህ ያለውን ሰው በየውሃት መንፈስ አቅኑት፤ አንተ ደግሞ እንዳትፈተን ራስህን ጠብቅ (ገላ 6፥1) ይላል ታዲያ ምን ያህል ጥንቃቄ የሚሻ ጉዳይ እንደሆነ ማሰብ አያዳግትም። መሸፈን ትኩረት የሚያስፈልገው ወሳኝ ጉዳይ ነው።

የሰው ልጅ ህልውና የሚቀጥለው በመሸፈን ውስጥ ነው። መዝሙረኛው ንጉስ ዳዊት ያልተሰራ አካሌን ዐይኖች አዩኝ ብሏል። ያልተሰራ ማንነታችንን እግዚአብሔር ሸፍኖን ነው የሚሰራን። አንድ ህንፃ ሲገነባ በለያዩ ምክንያቶች ዙሪያቸው ተሸፍነው ግንባታቸው ይከናወናል። ግንባታውን የሚቆጣጠረው መሃንዲስ ወይም ኢንጅነር የሚሰራውን ህንፃ መጨረሻ እያወቀው ነው መሰረት ጥሎ እስከ መጨረሻው ግንባታውን የሚያከናውነው። በውጭ የሚያየው ግን ህንፃው አልቆ ካላየው መጨረሻው አያውቀውም። አቤት እግዚአብሔር እጅግ መልካም አባት እኮ ነው። ጋርዶን ይሰራናል ስሙ ይባረክ።

እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው ምድሪቱን በከበበው በልጁ ክቡር ደም እንድንሸፈን ይፈልጋል። አዎ እርሱ ዓለምን በፍቅር ካጥለቀለቀው የክርስቶስ ደም ተሸፍነን እኛን ቀጥታ ሳይሆን በጌታ ኢየሱስ በኩል እንድንታይ ይሻል። ብቸኛው አርነት መውጫ ልጁ ነውና። ታዲይ በዚህ በገሀዱ ዓለም እንዴት እንሸፈን ብትሉ መፅሐፍ ቅዱሳችን በተደጋጋሚ የፅድቅ ልብሳችን የሆነውን ኢየሱስን ለብሰን እንድንመላለስ ያሳስባል።

ነገር ግን ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት
                                                        ሮሜ 13፥14

እግዚአብሔር አምላክ ፍቅር ነው። ፍቅሩም የዓለምን ኋጢአት በልጁ ደም ሸፍኖ የሚያኖር ደግ አባት ነው። እርሱ በራሱ ፍቅር ተመስርቶ የሚኖር አፍቃሪ አምላክ ነው። ፍቅር የሆነው እርሱ ደግሞ ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ብሎ በመፅሐፍ ነግሮናል በ1ኛ ጴጥ 4፥8። ከሁሉም ፍርድ እንድንድን የዘላለም ጠላታችን ከሆነው የወንድሞች ከሳሽ እንዲያፍር ያልተሸፈነ ማንነት አለን ብላችሁ የምታስቡ ፍፁም በሆነ መፀፀት ከኋጢአት ሁሉ በሚያድነው በጌታዬ ኢየሱስ ደም ሰውነታችሁን አጥባችሁ አዲሱን ልብሳችሁን ክርስቶስ ኢየሱስን ልበሱት። እግዚአብሔር የትናንት አይደለም የቅድሙን ማንነታችሁን አያይም ይልቁንም የአሁኑን ልባችሁን ነውና የሚያየው ደስ ይበላችሁ።

ምክር
ፊተኛ ኑሮአችሁን እያሰባችሁ እንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዱ፥ በአእምሮአችሁም መንፈስ ታደሱ፥ ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ።
                                                             ኤፌ 4፥22-24

Monday, 23 July 2018

ቅዱሱ መስዋዕት



እስራኤልን ከአራት መቶ ሰላሳ ዓመት በኋላ እግዚአብሔር ከግብፅ ባርነት እንዲያወጣቸው ያቀረበው መስዋት አንድ ነው (ዘፀ 12፥40 ጀምሮ)። ከነዚህ ሁሉ ዓመታት በኋላ ሌላ አርባ ዓመት የበረሀ ጉዞ ከፊታቸው አለ። ለዛውም እጅግ  አስቸጋሪ መንገድ። በረሀው የሚወክለው ይህን ዲያቢሎስ የሚገዛውን ዓለም ሲሆን የቀረበው መስዋት ደግሞ ጥላነቱ ጌታ ኢየሱስን ነው።

ሙሴና አሮን እንደታዘዙት መስዋቱን ካቀረቡ በኋላ በዚያው ቀን እግዚአብሔር የእስራኤልን ልጆች ከነሰራዊቶቻቸው ከግብፅ ምድር አወጣ። ከግብፅ ባርነት ቀንበር ነፃ አወጣ። ከፈታኝ የአርባ  ዓመታት ጉዞ በኋላ ወደ ተስፋይቱ ምድር ገቡ።

የሰው ልጅ ከነበረበት የኋጢአት ግዞት ወይም ከሞት ባርነት ግን ነፃ የሚያወጣው አንድ እውነተኛ ቅዱስ መስዋት ያስፈልገዋል። ከአዳምና ሔዋን መተላለፍ ጀምሮ የሰው ልጅ በዚህ እስራት ውስጥ ነበረ። ነገር ግን እስራኤልን ከግብፅ ባርነት እንዳወጣው የሰው ልጅንም ከዚህ የሚያወጣ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ የተወደደ የመአዛ ሽታ ቅዱስ መስዋት መታረድ አለበት። ይህም መስዋት የእግዚአብሔር አንድያ ልጅ ከኋጢአት በቀር በነገር ሁሉ እኛን የመሰለው የናዝሬቱ ኢየሱስ ነው።

ኢየሱስ ለዓለም የተሰዋ ሕዝቡንም ከሞት ባርነት ነጻ ያወጣ የነበረብንን ኩንኔ ያስቀረ። በደሙ ማስተሰርያ ይሰማን የነበረውን በደለኝነት ከላያችን ያነሳ ቅዱስ መስዋት ነው። እግዚአብሔር እስራኤልን መና ከሰማይ እያወረደ ሲራቡ እያበላ፣ ሲጠሙ ከዓለት ላይ ውሃ እያፈለቀ ጥማቸውን ቆረጠ። እኛ ግን ዛሬ በነገሮች ሁሉ በድካማችን የሚራራልን ሊቀካህናታችን፣ ተበልቶ ዳግም የሚያስርበውን ሳይሆን፣ የበረከት መና ሳይሆን የሕይወት እንጀራችን፣ ከአለቱ ፈልቆ እስራኤላዊያን ዳግም እንደተጠሙት ሳይሆን የሕይወት ውሃ የናዝሬቱ ጌታ ለእኛ ሰጠን።

እስራኤልም (የብሉይ ኪዳን ሕዝብ) እኛም (የአዲሱ ኪዳን ሕዝብ) የተሰጠን ከሰማይ ነው ልዩነቱ እነሱ የተሰጣቸው ከሰጪው የታዘዘላቸውን በረከት ሲሆን እኛ ግን ሰጪውን ነው፣ ምንጩን ነው ስሙ ይቀደስ። የበረከቱ እንጀራ ጊዜአዊ ነው የእኛ ግን ዘላለማዊ ነው።

የእስራኤል ህዝብ ተስፋይቱን ምድር ወርሰውም ለኋጢአት በየጊዜው ለእግዚአብሔር መስዋታቸውን ይሰዋሉ እኛ ግን በአንዱ መድሃኒት የዛሬ 2010 ዓመት የፈሰሰው ደም አሁንም ትኩስ ነው። አንዴ ለዘላለም ባፈሰሰው ደም ዘላለም ይቅር እያስባለ የሚኖር ቅዱስ መስዋት ነው። መፅሐፍም እንደሚል የልጁ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኋጢአት ሁሉ ያነጻል (1ኛ ዮሐ 1፥7)። ከዚህ ላይ ሌላ ለኋጢአት የሚቀርብ መስዋት የለም። ይህ ደም ለዘላለም በቂ ነው። እግዚአብሔር በኋጢአት ምክንያት እኛን ይቀጣ የነበረውን ፍርድ ሁሉ ጌታ መስቀል ከፍሎታል። ምንም ዓይነት ጌታ ለኋጢአት ያልከፈለው ዋጋ የለም።

ከምንም በላይ እጅግ ደስ ሊለን የሚገባው እግዚአብሔርን ያመኑ እስራኤላዊያን ተስፋ ያደረጉትን ምድር ከነአንን አገኙ እኛ ግን " በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤(የዮሐንስ ወንጌል 3: 36) ነው የተባለነው። እዳችንን ከፍሎ ወሰደን። ኢየሱስ ለኋጢአታችን ሞቶ ለጽድቃችን ከሙታን መካከል ተነሳ እኛንም በእርሱ የምናምን ሕያዋን አደረገን። አሁን በማያልፍ የሕይወት ኋይል በግርማው ቀኝ ባለበት በዚያ ስፍራችን ሆነ። በዚህም እጅግ ደስ ይበለን።
ዛሬም የኢየሱስ ደም ከኋጢአት ያነጻል።
ዛሬም የናዝሬቱ ጌታ ያድናል።
ዛሬም ሊቀካህናታችን በድካማችን ይራራል።
ዛሬም ኢየሱስ አልተወንም።

የእምነት ስሌት

ፒስቲስ በግሪክ ቋንቋ እምነት ማለት ሲሆን ትርጉሙም ሙሉ የልብ መሰጠት፣ በጥልቀት የተያዘ ከአመክንዮ ኋይል በላይ የሆነውን እግዚአብሔርን ማመን ማለት ነው። ከአህምሮአዊ እውቀት ወይም አቀባበል በላይ ማለት ነው። ፒስቲስ የመወሰን ትርጉምም አለው። የዚህ የፒስቲስ እምነት ያለው አንድ ሰው ስለ አንድ ነገር እውነት መሆኑን ጥልቅ በሆነ የልብ መሰጠት በመግባባት የተቀበለና በልበ ሙሉነት የሚጠብቅ ወይም እንደሆነ አድርጎ የደመደመ ሰው ማለት ነው።

የዕብራዊያን ፀሐፊ ሐዋርያው ጳውሎስ እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው።  (ወደ ዕብራውያን 11: 1) ይላል። የዚህ ዓይነት እምነት ለእግዚአብሔር መንግስት የተገባና ለመንግስቱም የመገበያያ ገንዘብ ነው።

ሰማያዊው ሀገር አሁን ባይታየንም ሀገር ሲሆን መገበያያውም እምነት ነው። በዚህ ዓለም ገንዘብ ሳይኖረን አንድ ነገር መግዛት እንደማንችል ሁሉ ካለእምነት ከሰማያዊ መንግስት ንጉስ ጋር ግንኙነት አይኖረንም ማለት ነው። ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም ተብሎ እንደተፃፈ።

የማታምነውን ነገር ለመቀበል አትችልም የማትጠባበቀውንም ነገር ለማየት አትችልም። ታዲያ ይህ እምነት የሚገበያየው ተስፋ ባደረገው ላይ በሚኖረው እምነት ነው። የሰው ልጅ በተፈጥሮ አንድን ነገር በመገመት   (predict በማድረግ ወይም ይሆናል በሚል) አውጥቶና አውርዶ ስለ አንድ ነገር ይወስናል። እምነት ያለው ሰው ግን ግምትን አይጠቀምም ይልቁንም እንደሚሆን ቆጥሮ በዛ ጉዳይ ላይ ይወስናል እንጂ። እግዚአብሔር ያደርገዋል የሚል የእምነት ገንዘብ መጠን አለው።

ሙሴ በንጉስ ፈርዖን ቤት እንደ ልዑል አድጎ ነገር ግን መፅሐፍ እንደሚል በእምነት ስሌት ልጅ መባልን አልፈለገም።

ሙሴ ካደገ በኋላ የፈርዖን የልጅ ልጅ እንዳይባል በእምነት እምቢ አለ፤ ከግብፅም ብዙ ገንዘብ ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍ እጅግ የሚበልጥ ባለ ጠግነት እንዲሆን አስቦአልና ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ፤ ብድራቱን ትኵር ብሎ ተመልክቶአልና።
                                          ዕብ 11፥24-26
እምነት ያለው ሰው በሚያየው ሳይሆን በሚያምነው ይኖራል። ሙሴ መጨረሻውን በእምነት አይቶ ጊዜአዊ ጥቅሙን ተው። አዎ ሙሴ እምነቱ ገንዘብ ሆነለት አሻግሮ መመልከት ስለቻለ መግዛት ያለበትን ገዛ። በምድር ላይ በሚያየውን ሳይሆን በእግዚአብሔር እውነተኛነት በእርሱም የተስፋ ቃሎች ላይ የተመሰረተ እምነት የነበረው ለእግዚአብሔር መንግስት የመግዛት አቅም እንዲኖረው አደረገ። እምነት ያሰላል!!!

ኖህንም ብንመለከት
ኖኅ ገና ስለማይታየው ነገር ተረድቶ እግዚአብሔርን እየፈራ ቤተ ስዎቹን ለማዳን መርከብን በእምነት አዘጋጀ፥ በዚህም ዓለምን ኰነነ፥ በእምነትም የሚገኘውን ጽድቅ ወራሽ ሆነ።
                                                    ዕብ 11፥7                         

 እግዚአብሔር መርከብ እንዲሰራ ሲያዘው ኖህ አንድም የዝናብ ጠብታ ሳያይ ነው መርከብ የሰራው። በጠራራ ፀሐይ መርከብ ሲሰራ ያዩት ሁሉ እንደ እብድ ሳይቆጥሩትም አልቀሩ። እንኳን መርከብ ይቅርና ዝናብ ይዘንባል ብለህ ተማምነህ ዣንጥላ ይዘህ ሲያዩህ እንደታመምክ ሊቆጥሩህ ይችላሉ። ኖህ እነሱ የማያውቁትን እሱ በእርግጠኝነት አውቋል። ምክንያቱም እምነቱ ተስፋ የሚያደርገውን እውነት በእምነት ስሌት አስልቶ ገዝቶት ነበረና። እምነት ያሰላል።

በብዙ ችግር ውስጥ ያላችሁ፣ ተስፋ የምታደርጉት የማይመስል ለሆነባችሁ፣ በይሆናልና አይሆንም መካከል ውስጥ ለተቀመጣችሁ፣ አሁን በዓለም በምታዩት ነገር ተወስዳችሁ ብሩኩ ተስፋችንን የዘነጋችሁ እምነት ያሰላል። በማስላት ወደሚገኝ ክብር የሚያመጣ በእምነት መገበያያ ገንዘብ እንያዝ አላለው። በድጋሚ እምነት ያሰላል።

ደግሞም በኑሮአችሁ ሰልፍ በዝቶባችሁ ላላችሁ፣ አንዳች ነገር እንዲሰጣችሁ እግዚአብሔርን ጠይቃችሁ መልስ በመጠበቅ ላይ ላላችሁ፣ በእግዚአብሔር በረከት ላይ ሳይሆን በበረከቱ አምላክ፣ በበረከቱ ሰጭ፣ ወይም በበረከቱ ምንጭ እግዚአበሔር ላይ ባለ እምነት ላላችሁ ይህ የመንግስቱ መገበያያ ገንዘብ እንዳይባክን ፀንታችሁ እንድትቆዩ እያሳሰብኩ በእምነት የገዛችሁት ይሆናል፣ በእርግጥ እግዚአብሔር ታማኝ ነውና ያደርገዋል። በእምነት አስልታችሁ በያዛችሁት ተስፋ እንድትፀኑም ምክሬ ነው። በእምነት ማስላት መኖራችሁን ቀጥሉበት አላለው።

እምነት ያሰላል!!!
ይህን መልእክተ እኔ ፃፍኩት እናንተም አንብባችሁ ሼር በማድረግ ሌሎች እንዲማሩበት እንድታደርጉ በጌታ ፍቅር እጠይቃለው። ቪዲዮውን መመልከት አይርሱ። እኔ ተባርኬበታለው እናንተንም ይጠቅም ዘንድ እነሆ ጋበዝኳችሁ። ለመጠቀምም ለመጥቀምም ሆናችሁ ትመለከቱት ደግሞም የእግዚአብሔር ቃል ሊነግረን በፈለገው መጠን መረዳት ይሆንላችሁም ዘንድ ፀሎቴ ነው።

አጽናኑ



'' አጽናኑ፥ ሕዝቤን አጽናኑ ይላል አምላካችሁ። ''
                                                 ኢሳ 4፥1

በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደምናነበው እስራኤል በባቢሎን ለሰባ ዓመታት በምርኮ ስትወድቅ ከፍተኛ መንፈሳዊ ክስረት ደርሶባታል። በዚህም ምክንያት በንጉስ ሰለሞን በከበሩ ድንጋዮች የተሰራው ቤተመቅደስ በባቢሎናዊያን በመቃጠሉ መቅደስ አልባ  ለመሆን ችለዋል። የእግዚአብሔር ታቦትም ተማረከ፣ ብዙ መጻህፍትም በእሳቱ ተቃጠሉ። ሌሎችም ክስረቶች ደርሶባቸው ነበር እናም የደረሰባቸውን መከራና የነፃነት እጦት ምክንያት ተስፋ ወደ መቁረጥ በመድረስ

'' መንገዴ ከእግዚአብሔር ተሰውራለች ፍርዴም ከአምላኬ አልፋለች ''
 (ትንቢተ ኢሳይያስ 40: 27)  በማለት አጉረመረሙ።

ነገር ግን እግዚአብሔር ሰሚ ነው ታምፆበትም ይሰማል። እርሱ ታማኝ እረኛ ነው ሕዝቡን አልተወም አጽናኝ ነብያትን በመላክ ሕዝቡን ያጽናና ነበር። ከላይ ከጠቀስነው ከኢሳያስ ምዕራፍ አርባ በኋላ የነበሩት ትንቢቶች ስለ ነፃ አውጪው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መሲህነት ነው። እስራኤልም መሲሁን በተስፋ ይጠብቁት ነበር። ነገር ግን መፅሐፍ እንደሚል

'' የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም። '' (የዮሐንስ ወንጌል 1: 11)

ዛሬ በዘመናችን የሰው ልጅ በልዩ ልዩ ምርኮ ውስጥ ወድቋል መሲሁ ክርስቶስ ኢየሱስ ለኋጢአት ሞቶ ደግሞም እኛኑን ስለማፅደቅ በመነሳት የምስራች እየተነገረ ባለበት በዚህ ዘመንም የሰው ልጅ በሌሎች ነገሮች ተማርኳል። ዘመኑ በቴክኖሎጂ የላቀ ደረጃ ላይ የደረሰበት በመሆኑ ሰዎች በቀላሉ መረጃ የሚያገኙበት ዘመን ላይ እንገኛለን።

ከዚህም የተነሳ ራሱንና አጠገቡ ያለውን በመዘንጋት የሩቁን የመረጃ ዜናዎች በመስማትና በማንበብ ተጠምዶአል። አብዛኞቹ የመረጃ መገናኛ አውታሮች ትኩረት የሚስብ ትኩስ ዜና ካጡ ስራ የሰሩ አይመስላቸውም። መልካሙን እየተዉ የጭንቀት ወሬ ለማግኘት የሚያነፈንፉ ብዙዎች ናቸው። አንድ አደጋ ወይም ጦርነት ወይም አንዳች እልቂት ያለበት መረጃ ካገኙ ሁሉም ያንኑ ክፉ ወሬ እንደ በግ ሲያመነዥጉት ይሰነብታሉ። የሚያጽናናም ሆነ የሚያንጽ ወሬ የሚነገርበት ወይም የሚነበብበት የመረጃ አውታሮች እጅግ ጥቂት ናቸው።

አሁን ሁላችንም ማለት በሚቻል ሁኔት በሞባይል ስልካችን ኢንተርኔትን በመጠቀም ለመረጃ ቅርብ ነን። በተለይ በFacebook። ወደዚህ መንደር የገባን እንደሆን ብዙ አሉባልታ ያለበት ዜና እንደአሸን የፈላ ነው። ድሮ ሐሜት አለ ተብሎ የምንሰማው ቡና ሲጠጣ ነበር አሁን ግን በፈረደበት በFacebook ሆኗል። በግለሰቦች ደረጃ የነበረው ሐሜትና ውሸት አድጎ ብሔራዊ ብሎም ኢንተርናሽናል አድርገነዋል።  በጣም የሚገርመው በፊት ብና እየተጠጣ ያለ ክፍያ የሚወራው ወሬ ዛሬ ላይ ኢንተርኔት ለመጠቀም ገንዘብ አውጥተን ካርድ በመግዛት በጀተኛ ሐሜተኞች ሆነናል።

ስለ ሰዎች ክፋትና በደል ብዙ የሚፃፍበት ነገር ግን ስለ ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት ጥቂት መፃፍ የሚያሰተችበት ዘመን ላይ ነን። ስለ ሰዎች ማንነት ለሰዓታት እናወራለን ነገር ግን መፅሐፍ ቅዱስ ይዘን አንድ ምዕራፍ ክርስቲያናዊ በሆነ መንገድ መነጋገር አቅቶናል።

የአንድን የእግር ኳስ ብድን ተጫዋቾች በሙሉ ከነመለያ ቁጥራቸው ሸምድደን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት የተነገሩበትን የመፅሐፍ ቅዱስ ክፍል ግን አንብበን የማናውቅ እንኖራለን።

እግዚአብሔር ፈቅዶለት ጸጋውም አስችሎት ጥቂት የሚፅፈውን ወይም የሚመሰክር ሲመጣ የሀሰት ስም በመለጠፍ የተፃፈው አጀንዳ ተረስቶ ወደ ሰውዬው ማንነት Divert ያደርጋል። የጉብዝናዬ ወራት ሳያልፍ ፈጣሪዬን ላስብ ብሎ ወደ እግዚአብሔር ቃል ያዘነበለን ሰው በመከፋፈልና በማሳት ወደ ፀብና ትችት እንዲያደላ የምናደርገው ለምንድነው?

በጣም የሚገርመኝ ነገር ቢኖር አንድ ጊዜ አንድ የራሴን ፎቶ በዚሁ የFacebook Wall ላይ ለጠፍኩኝ እናም የሚያውቁኝ ሁሉ የተለመደውን Like አልፎ አለፎም Comment አደረጉ በሚቀጥለው ቀን ግን አንድ የእግዚአብሔር ቃል ከነጥቅሱ ለጠፍኩኝ እነዛ Likeዎች ድራሻቸው ጠፋ ምክንያቱም ከእኔ ባሻገር ያለውን መልእክት መመልከት ስላልቻሉ። ከላይ የጠቀስኩት መከፋፈል ያመጣው መዘዝ መሆኑ ነው።

መዝሙረ ዳዊት ምዕራፍ አራት ቁጥር ስድስት ላይ በጎውን ማን ያሳየናል? የሚሉ ብዙዎች ናቸው ይላል። ብዙዎች ለዚህ ለሚያልፈው ዓለም ሳይሆን ከጌታ ጋር ዘላለም የምንኖርበትን መንገድ ማወቅ ይሻሉ። እርስ በእርሳችን በፍቅር እንደ እግዚአብሔር ቃል ካልተገሳጸጽን፣ ተስፋ የቆረጠውን ካላጽናናን እንዴት የጌታ ፍቅር ገባን ልንል እንችላለን?

በዚህ ቃል ተጽናኑ (1ኛ ተሰ 4፥18)

እግዚአብሔር በልጁ በክርሰቶሰ ኢየሱስ ያመንን ሁላችን እርስ በራሳችን እንድንጽናና ይፈልጋል። እንድንደጋገፍ አንዱ ለሌላው አበርታች እንድንሆን ይሻል። ታዲይ ምንድነው የምንጠብቀው? ጥፋት ያለበት አንድ ሰው ቢገኝ ቃሉ እንደሚያዘው በየዋሃት መንገድ ማቅናት አንድም እሱን ለመጥቀም አንድም እኛም እንዳንሰናከል ለምን እንደ ቃሉ አንሆንም?

አጽናኙ ለዘላለም ከእኛ ጋር ነው።
(ዮሐ 14፥15-16፣ ዮሐ 14፥26፣ ዮሐ 15፥26)

የሚያጽናናን የእግዚአብሔር መንፈስ፥ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ፥ የምክርና የኃይል መንፈስ፥ የእውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ተልኮልን ለእርሱ እንዳንገዛ አዚም ያደረገብን ማን ነው? መሲሁ ክርስቶስ ስለእኛ መስዋህት ሆኖልን የእኛ መዘናጋት ጤነኝነት አይደለም። ለእስራኤል የተላኩት የምርኮ ዘመን ነብያትን ነው ለእኛ ግን ታላቅ አጽናኝ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው። እጅግ እድለኞች ነን። መጽናናት ይሁንልን።

ይህንን ፅሁፍ ላነበባችሁ በሙሉ አንዳችን ለአንዳችን መኖር ይገባልና በሰው ልብ ውስጥ ጥላሸት ከምንቀባ አንድ የእግዚአብሔር  ቃል ተናግረን ሰውን አጽናንተን በብሩኩ ተስፋችን በጌታ ኢየሱስ ላይ ባለ እምነት እንዲኖር የሁልጊዜ ኑሮአችን እናድርግ እላለው። የማንችል ነን ብላችሁ ለመሞከር በፍርሃት ያላችሁ አዎ ሁላችን አንችልም ነገር ግን የሚያስችል ፀጋ በሚያስፈልገን ጊዜ ይሰጠናልና። የእግዚአብሔር ቃል እንደሚል '' ሰው በኋይሉ አይበረታምና '' በራሳችን ሳይሆን በፀጋው ላይ በመውደቅ የሚገኝ አገልግሎት ይኖረን ዘንድ ሰዓቱ አሁን ነው። አረፈደም ዘመኑ ካመጣው መንፈሳዊ ክስረት እንውጣ።

የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ፀጋ የእግዚአብሐር አብ ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ህብረት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን።
ሼር

የሚታይ እምነት



በእግዚአብሔር ቅዱስ ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለንን እምነት የውስጥን ከሚያውቀው ከእርሱ በቀር ማንም ሊይውቅ አይችልም። እርሱ ዓይኖቹ እንደ እሳት ነበልባል የሚያበሩ ልብና ኩላሊትን የሚመረምሩ፣ ስለ ሰዎች ሊነገረው የማይገባ ሁሉን የሚያውቅ ከልባችን ይልቅ ታላቅ የሆነ እርሱ ብቻ ነው። ሰው ስራን ወይም ውጫዊ የሆነውን ድርጊት ብቻ ያያል እርሱ ግን የልባችንን ያውቃል። ቃላት ሳንተነፍስ መልስ የሚሰጥ ቸር እረኛ ነው።

እምነት በስራ ይገለጣል ነገር ግን በስራ መገለጡ የሚጠቅመው መልሶ ራሳችንን ወይም በዘንዳችን ያሉትን ሰዎች ነው። ምክንያቱም እግዚአብሔር ስለ እኛ ለማወቅ ብሎ የሚፈትነን ነገር የለም። እርሱ አስቀድሞ አውቆናልና። ይልቅስ እምነታችን እንዲታይ የሚፈለግበት ምክንያት ከላይ የጠቀስኩት የራሳችንን እምነት ጥንካሬ እንድንፈትሽ ወይም የእምነታችንን አነሳሳሽ ምክንያት በእኛ እንዲገለጥ እና ለሌሎች ምሳሌ እንድንሆን ነው።

አብርሃም ልጁን ይስሀቅን እንዲሰዋ እግዚአብሔር ሲያዘው እግዚአብሔር አብርሃም በእምነት እንደሚታዘዝ ሳያውቅ ቀርቶ አይደለም። ኢዮብን ሰይጣን እንዲፈትነው እግዚአብሔር የፈቀደው የኢዮብን መታመን ሳያውቅ ቀርቶም አይደለም። ነገር ግን እነዚህ ሁለቱ የእምነት ሰዎች በእግዚአብሐር ላይ ምን ያህል እንደተደገፉ ራሳቸው አያውቁም ነበረ። ሰይጣን ኢዮብን ስለባረከው ነው እግዚአብሔርን የተከተለው በማለት ከሰሰና ተፈቀደለት። ተፈተነም ብዙ ነገሩን አጣ ነገር ግን ኢዮብ በበረከቶቹ ላይ ሳይሆን በበረከቶቹ አምላክ እምነት እንዳለው እርሱም አወቀ እኛም ይኧው እየተማርንበት እንገኛለን። የሚታይ እምነት አሳየ።

በማርቆሰ ወንጌል ምዕራፍ ሁለት ከቁጥር አንድ እስከ አምስት ድረስ ያለውን ብንመለከት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እምነትን በማየት ኋጢአት ሲያስተሰርይ እናነባለን። 

ከጥቂት ቀን በኋላ ወደ ቅፍርናሆም ደግሞ ገብቶ በቤት እንደ ሆነ ተሰማ። በደጅ ያለው ስፍራም እስኪጠባቸው ድረስ ብዙ ሰዎች ተሰበሰቡ፤ ቃሉንም ይነግራቸው ነበር። አራት ሰዎችም የተሸከሙትን ሽባ አመጡለት። ስለ ሕዝቡም ብዛት ወደ እርሱ ማቅረብ ቢያቅታቸው እርሱ ያለበትን የቤቱን ጣራ አነሡ፥ ነድለውም ሽባው የተኛበትን አልጋ አወረዱ። ኢየሱስም እምነታቸውን አይቶ ሽባውን። አንተ ልጅ፥ ኃጢአትህ ተሰረየችልህ አለው።
                                                    (ማር 2፥1-5 )

የማርቆስ ወንጌል ክርስቶስን እንደ አገልጋይ አድርጎ የሚያሳይ የመፅሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው። በዚህ ምዕራፍ ውስጥም በአንድ ቤት ውስጥ እንዴት ባለ ትህትናና ዝቅታ ጌታ ኢየሱስ ያስተምር እንደነበር ያሳያል። እነዚህ አራት ሰዎች እርሱ ያገለግል ወደ ነበረበት ቤት ሲመጡ መግቢያ መንገድ ባለመኖሩ አልተመለሱም። እርሱን እንጂ እርሱ ከገባበት ቤት ጋር ጉዳያቸውን አላዛመዱም፣ ግድግዳ አልዳበሱም፣ የገባበትን መንገድ የረገጠውን መሬት አላሉም፣ ኋጢአተኛ የሚያስፈልገው መድሃኒት እርሱ ኢየሱስ  ጋር ብቻ ሲደርስ እንደሆነ አምነዋል። ማድረስ የነበረባቸው አካል ጋር አደረሱት ተፈወሰም። የሚከተሉትን ደቀ መዛሙርትን እንኳ ጥሩልኝ አላሉም ምክንያቱም ኋጢአት ሊነፃ የሚችለው በጌታ ኢየሱስ ብቻ ነው ስሙ ይቀደስ።  የሚታይ እምነት ይሏል ይህ ነው።

ጌታ ኢየሱስ ጋር ለመድረስ ማድረግ ያለባቸውን አደረጉ በሩ ቢጨናነቅም ጣራ አንስተው ከላይ ወደ ታች ሽባውን አስገቡት እርሱም ስራቸውን ሳይሆን እምነታቸውን በማየት የሽባውን ልጁ ኋጢአት ይቅር አለ። አዎ እኛ የአራቱን ሰዎች  ስራ ላይ ትኩረት እናደርግ ይሆናል እርሱ ግን እምነትን ያያል። እኛ ልፋታቸውን አይተን ክንፈረ እንመጥ ይሆናል ነገር ግን እርሱ የመጡበትን ዓላማ ያውቃል።

እነዚህ አራት ሰዎች ተሸክመው በማምጣት ኋጢአተኛውን ከመድሃኒቱ ጋር አገናኙ። ዛሬ ላይ የክርስቶስ ኢየሱስ ነን እያሉ መንገድ የዘጉ ብዙዎች አሉ። በክርስቶስ ኢየሱስ ላይ ባላቸው እምነት ሳይሆን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ወይም ስርአት ተመርኩዘው እነሱም ሳይደርሱ ሰውንም ተሸክመው ሳያደርሱ በር ዘግተው የተቀመጡ ብዙዎች አሉ። እኛስ የቱ ጋር ነን? ራሳችንን እንፈትሽ።

አብዛኛው ህዝብ እረፍት ፍለጋ ሲባዝን እያዩት የተስፋውን ቃል ከመንገር ይልቅ በሃይማኖታዊ ካባ ሽፋን በሁከት ድምፅ እያሸበሩ ከመድሃኒቱ ጋር እንዳይገናኝ ታክል የሆኑ ብዙዎች አሉ። እኛስ የቱ ጋር ነን?

እርሱ ሁሉ አዋቂ ነው። አሁን እንኳ ይህን እየፃፍኩ እናንተም እያነበባችሁ በምን ዓይነት ልብ እንዳለን ያውቃል። ተሽክሙ ጣራ አንሰተው ነድለውም በሽተኛን ወደ መድሃኒቱ የሚያመጡበት ባለበት ስፍራ እንኳ ተቃዋሚዎች ነበሩ። ኋጢአትህ ተሰረየችልህ ስላለው ስለምን እንዲህ ያለ ስድብ ይሳደባል ነበር ያሉት። ዛሬም በማያልፍ የሕይወት ኋይል በግርማው ቀኝ የተቀመጠውን ጌታ ጋር ሰዎች እንዲደርሱ ሰዎችን መሸከም አለብን። የሚታይ እምነት ይኑረን እርሱ አሁንም የልባችንን ያያል። አዎ

ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትና ዛሬ እስከ ለዘላለምም ያው ነው።
                                                       (ዕብ 13፥8)

በእርሱ ዘንድ የሚታይ እምነት ይጨምርልን። የጌታ ኢየሱስ ሰላምና ፍቅር ይብዛላችሁ። አሜን።

ያ ሰው



ያ ሰው እኔ ነኝ የበደልኩትኝ
ያ ሰው ኢየሱስ ነው እኔን ያዳነኝ

እኔ:-
ንጉስ ዳዊት ኣሪዮንን ካስገደለ በኋላ እግዚአብሔር  በናታን በኩል ተናገረው ላደረገውም ኋጢአትን የመሸፈን ስራ ለራስህ ብዙ ሰጥቼ ሳለ አንተ ግን አልበቃህ ብሎ የሰውን ወሰድክ። ላደረከውም ክፉ ስራ ሌላ የበደል ካባ ደረብክ፣ የሰጠውህ አንሶም ከሆነ እጨምርልህ ነበር ነገር ግን አልጠየከኝም ብሎ ዳዊትን ወቀሰው። ሁለተኛ ሳሙኤል ምዕራፍ አስራ ሁለት ከቁጥር 1-7 እንዲህ ይላል:-

እግዚአብሔርም ናታንን ወደ ዳዊት ላከ ወደ እርሱም መጥቶ አለው። በአንድ ከተማ አንዱ ባለጠጋ አንዱም ድሀ የሆኑ ሁለት ሰዎች ነበሩ። ባለጠጋውም እጅግ ብዙ በግና ላም ነበረው። ለድሀው ግን ከገዛት አንዲት ታናሽ በግ በቀር አንዳች አልነበረውም፤ አሳደጋትም ከልጆቹም ጋር በእርሱ ዘንድ አደገች፤ እንጀራውንም ትበላ፥ ከዋንጫውም ትጠጣ፥ በብብቱም ትተኛ ነበር፥ እንደ ልጁም ነበረች። ወደ ባለጠጋውም እንግዳ በመጣ ጊዜ ከበጉና ከላሙ ወስዶ ለዚያ ወደ እርሱ ለመጣው እንግዳ ያዘጋጅለት ዘንድ ሳሳ፤ የዚያንም የድሀውን ሰው በግ ወስዶ ለዚያ ለመጣው ሰው አዘጋጀ። ዳዊትም በዚያ ሰው ላይ እጅግ ተቈጥቶ ናታንን። ሕያው እግዚአብሔርን! ይህን ያደረገ ሰው የሞት ልጅ ነው። ይህን አድርጎአልና፥ አላዘነምና ስለ አንዲቱ በግ አራት ይመልስ አለው። ናታንም ዳዊትን አለው። #ያ_ሰው_አንተ_ነህ።

አዎ ያ ሰው አንተ ነህ አለው። በራሱ ላይ የፈረደ በሰው ሲሆን በደሉ የገባው ራሱን በጉዳዩ  ውስጥ ሳይመለከት በሰው ውስጥ ሲሆን የነገሩን ታላቅነት ተረዳ ፈረደም። እግዚአብሔር በምሳሌ ንጉስ ዳዊትን ገሰፀው። እኔም በዚህ የታሪክ ክፍል ብዙ ተማርኩ ጉዳዩን ወደ ራሴ አመጣሁት። እኔስ ብሆን ብዬ ራሴን በዚህ ታሪክ ውስጥ አገኘው።

ያ ሰው እኔ ነኝ። ሁሉ ተሰጥቶኝ፣ የጎደለብኝ ሳይኖር በክቡር የክርስቶስ ደም ተገዝቼ፣ ውድ ዋጋ ወጥቶብኝ ሳለ ነገር ግን እኔ በበደሌና በኋጢአቴ ሙታን ነበርኩኝ፣ የሥጋዬንና የልቡናዬን ፈቃድ እያደረኩ  በሥጋ ምኞት በፊት እኖር ነበር፣ ከፍጥረቴ ጀምሮ የቁጣ ልጅም ነበርኩ። በአለመታዘዝ ጠንቅ የጠፋው፣ በዓለም ተወስጄ ከእግዚአብሔርም ክብር ጎድዬ ከመንፈሱ እርቄ የምኖር ተቅበዥባዥ ነበርኩ። መንፈሳዊ ካባ ደርቤ፣ ለሚያየኝ አማኝ መስዬ፣ የራሴን የመዳን መንገድ ፈፅሜ ቤዛዬ ላይ ደርቤ፣ ከበደልና ከኩነኔ የሚያነፃውን ክቡር ደሙን አክፋፍቼ የነበረ፣ አዎ ያ ሰው እኔ ነኝ። ነገር ግን.........

ኢየሱስ:-

በኢየሩሳሌምም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ቤተ ሳይዳ የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፤ አምስትም መመላለሻ ነበረባት። በእነዚህ ውስጥ የውኃውን መንቀሳቀስ እየጠበቁ በሽተኞችና ዕውሮች አንካሶችም ሰውነታቸውም የሰለለ ብዙ ሕዝብ ይተኙ ነበር። አንዳንድ ጊዜ የጌታ መልአክ ወደ መጠመቂያይቱ ወርዶ ውኃውን ያናውጥ ነበርና፤ እንግዲህ ከውኃው መናወጥ በኋላ በመጀመሪያ የገባ ከማናቸው ካለበት ደዌ ጤናማ ይሆን ነበር። በዚያም ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፤ ኢየሱስ ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ፥ እስከ አሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ። ልትድን ትወዳለህን? አለው። ድውዩም። ጌታ ሆይ፥ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል ብሎ መለሰለት። ኢየሱስ። ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለው። ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ።
ያም ቀን ሰንበት ነበረ። ስለዚህ አይሁድ የተፈወሰውን ሰው። ሰንበት ነው አልጋህንም ልትሸከም አልተፈቀደልህም አሉት።
እርሱ ግን። #ያዳነኝ_ያ_ሰው። አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለኝ ብሎ መለሰላቸው።
                                                               ዮሐ 5፥2-11

አዎ ጌታ ኢየሱስ በድካሜ የሚራራ መልካሙ እረኛዬ፣ የዓለምን ኋጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ፣ ክብሩን እንደመነጠቅ ሳይቆጥር ከዙፋኑ ወርዶ እንደ እኔ ሰው ሆኖ፣ ከባዱን ሸክሜን ሊሸከም፣ ስለ ኋጢአቴ ልከፍለው የሚገባውን የመስቀል ሞት ስለእኔ ሊሞት፣ የእኔን መራራ ፅዋ ሊጠጣ ራሱን አሳልፎ የሰጠው የእኔ አዳኝ፣ የዓለም ቤዛ ያዳነኝ ያ ሰው ኢየሱስ ነው።

ሰው የለኝም ብሎ የነበረው ድውዩም እውነተኛውን ኋጢአት የሌለበት፣ ነውር የማያውቀው፣ ስለ እኛ የመጣውን ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ አገኘው ዳነም። ዛሬም እኔ ከዘመናት በፊት በከፈለልኝ ውድ ዋጋ ድኛለው። በክርስቶስ ኢየሱስ በሆነው ቤዛነት በኩል በፀጋው ሕያው ሆኛለው። እረ እኔስ ሰው አለኝ። የዘላለም ሊቀካህኔ ኢየሱስ፣ በእኔና በእግዚአብሔር መካከል ያለ መካከለኛዬ፣ እረ እኔስ ሰው አለኝ።

ማሳሰቢያ:-
ይህን ፅሁፍ ላነበባችሁ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍፁም ሰው ፍፁም አምላክ መሆኑን ሳትዘነጉ መሆን ይኖርበታል።
የጌታ ፀጋና ሰላም ለሁላችን ይብዛልን አሜን።

ቆራሌው



ከልጅነታችን ጀምሮ የቆራሌን ድምፅ በመስማት አድገናል። ገና ከሩቅ ሆኖ '' ቁራሌው አሮጌ ጫማ ያለው '' እያለ ሲጮህ ሰምተናል። አንዳንዴ ጠብቁት ተብለን አልያም ሲመጣ ጥሩን ተብለን የቆራሌውን ድምፅ ለመስማት ጆሮዎቻችንን አንግበን የጠበቅንበት ጊዜአትም አሉ።

ቆራሌው ሰዎች የተጠቀሙበትን አሮጌ እቃ በየሰፈሩና በየመንደሩ በመግባት እየሰበሰበ በርካሽ ዋጋ የሚገዛ እግረ ቀጭን ሰው ነው። ይጠቅመኛል ያለውን እቃ እየመረጠ የሚስማማውን ዋጋ በመጥራት ይደራደራል። ቆራሌው ከሚደራደርበት መንገድ አንዱ የሚገዛውን እቃ ማጣጣል ነው። የማይጠቅም አድርጎ ወይም በጣም የተጎዳ በማድረግ በሚፈልገው ዋጋ ለመግዛት የሚጠቀምበት ስትራቴጂ ነው።

ሻጭም ስለገዛ እቃው የነበረውን ግምት ወይም ዋጋ በማሳነስ በቀላሉ ለቆራሌው በአነስተኛ ዋጋ ይሸጣል። የሰው ልጅም አእምሮው ትንሽ ያረገውን ነገር ለመተው አይቸገርም።   የማይጠቀምበትን እቃዎች በሙሉ እንደ ቅራቅንቦ በመቁጠር አሳልፎ የባለቤትነት መብት ለቆራለው ይሰጠዋል።

የሰው ልጅ በክርስትና ሕይወቱ የሚፈትኑት ሶስት ነገሮች አሉ። እነዚህ በሕይወቱ ሁሉ ጠላቶቹ የነበሩና አሁንም ድረስ ያሉ የዘላለም ጠላቶቹ ናቸው።
1) ሀሰተኛ የሀሰት አባት ዲያቢሎስ
2) ይህ የምንኖርበት ዓለም
3) ተሸክመን የምንዞረው ስጋችን ወይም የሰጋ ሰሜት ናቸው።

እኛ ሰዎች ከፍተኛ ውጊያ የምናደርገው አእምሮአችን ውስጥ ነው። እነዚህ ከላይ ያየናቸው ደግሞ ሀሳባችንና እንቅስቃሴአችንን በመቆጣጠር ሰው ከተፈጠረበት ዓላማ ውጪ እንድንሆን ያደርጉናል። ከእውነት ይልቅ በምናየውና በአእምሮአችን የእውቀት ደረጃ መጠን ብቻ ነገሮችን እንድናይ ይገፋፉናል። ሶስቱም በጌታ ያለውን ሰላም እንዳንይዝ፣ እረፍት እንዳይሰማን፣ ንስሀ እንዳንገባ በመከላከል የሚያጠቁን የፅድቅ ጠላቶቻችን ናቸው።

እንደ ሥጋ ፈቃድ የሚኖሩ የሥጋን ነገር ያስባሉና፥ እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚኖሩ ግን የመንፈስን ነገር ያስባሉ።
ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፥ ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው። ስለ ሥጋ ማሰብ በእግዚአብሔር ዘንድ ጥል ነውና፤ ለእግዚአብሔር ሕግ አይገዛምና፥ መገዛትም ተስኖታል፤ በሥጋ ያሉትም እግዚአብሔርን ደስ ሊያሰኙት አይችሉም።
                                                   ሮሜ 8፥5-8

ይህ ያልተቤዠው ስጋችን ከቀድሞው ጠላት ዲያብሎስ ምክር በመቀበልና በክፉ ከተያዘው ከዚህ ከአሁኑ ዓለም በሚያየውና በሚሰማው እየተታለለ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን እንቅፋት ይሆንብናል። ወደ እግዚአብሔር ፍፁም ሙላት እንዳንደርስ የሚጎትት የሞት ሀሳብ ወደ ልባችን ሹክ የሚል እንቅፋት ነው። የበደለኝነት ስሜት እንዲሰማን በማድረግ ከእግዚአብሔር ይቅርታ እንዳንጠይቅ በደላችን በደልን ከሚያነፃ ከክርስቶስ ደም የላቀ እንዲመስለን የሚያደርግ የክፉት ሽኩሽክታ ነው።

ይህ የስጋ ስሜት የሚሰማው ድምፅ አለ የወቃሽ ድምፅ። እንደ ቆራሌው አሮጌውን ማንነት የሚያስታውስና ወደ ኋላ የሚጎትት ድምፅ። ልክ እንደ ቆራሌው የመግዣ ስትራቴጂ ያጣጥልሃል፣ ለራስህ ያለህን ዋጋ እንዳታስተውል የኋጢአትህን መአት ያዥጎደጉድልሃል፣ ራስህን በመውቀስ የኩነኔ ስሜት እንዲሰማህ ያደርግሃል፣ ስለአንተ የፈሰሰ ደም እንዳለ ያስረሳሃል፣ ኋጢአትህ የማይነፃ እስኪመስልህ ድረስ ዋጋ ቢስ ያደርግሃል፣ በሕይወትህ ተስፋ በማስቆረጥ የፅድቅ ወጋገንን ይሸፍንብሃል፣ የኢየሱስ ክብር ደም ከኋጢአት ሁሉ እንደሚያነፃ ከህሊናህ ውስጥ ይሰውራል።
'' አንተ እኮ እንዲ አድርገሃል እንዴት ንስሀ ትገባለህ ''
'' የአንተ በደልማ ይቅርታ አያሰጥም ''
'' አሁን አንተ ነህ ክርስቲያን የምትሆነው '' በማለት ይወቅሳል። ነገር ግን መፅሐፍ እንደሚል

ነውር የሌለው ሆኖ በዘላለም መንፈስ ራሱን ለእግዚአብሔር ያቀረበ የክርስቶስ ደም እንዴት ይልቅ ሕያውን እግዚአብሔርን ልታመልኩ ከሞተ ሥራ ሕሊናችሁን ያነጻ ይሆን?
                                                              ዕብ 9፥14
ከምን ያህል የሞተ ስራ ህሊንችንን የሚያነፃ የኢየሱስ ደም ብቃት እንዳለው ይናገራል። ከየትኛውም በደልና ኋጢአት የሚያነፃ ውድ ደም አለ። ለዚህም ነው የልጁ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኋጢአት ሁሉ ያነፃል ተብሎ የተፃፈው።

ስለዚህ ተወዳጆች ኢየሱስ የሞተው ስለኋጢአታችን ነው። እርሱ ህሊናን ከሞተ ስራ ያነፃል። መንፈሳዊ ቆራሌው የሚለውን አትስሙ። እርሱ ሊሰርቅ ሊያርድ እንጂ ስለሌላ አልመጣምና ''  ቆራሌው በደለኛ ስሜት ያለው '' ሲላችሁ በኢየሱስ ስም ተቃወሙት። ክፉውን ተቃወሙት እርሱም ከእናንተ ዘንድ ይሸሻል ተብሎ ተፅፏልና።

የቱንም ያህል በደል ቢኖርብን ሁሌ ለጥቅማችን የሚጠራን ድምፅ አለ። በጎቼ ድምፄን ይሰማሉ ይከተሉኝማል እንዳለ ጌታ ይህን ድምፅ ብቻ መስማት ይሁንልን። እናንተ ደካሞች ሸከማችሁ የከበደ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለው የሚል ብርቱ ድምፅ አለ።

አሮጌ እቃ የሚገዛው እግረ ቀጭኑ ቆራሌው አሮጌዎቹን ሰብስቦ ጥቂትም ቢሆን ብር ከፍሎ ይሄዳል ይሄኛው መንፈሳዊ ቆራሌ ግን ያለመታከት የሚሰራ ኩነኔ ወይም የባሰ የበደለኝነት ስሜት ጨምሮ  የሚሄድ አፍዝ አደንግዝ የዘላለም ጠላታችን ነው። ራሳችንን በማርከስ አእምሮችንን አንስጥ፣ አንገዛለት አላለው። ይህን እንድናደርግ በሚያስፈልገን ጊዜ ሁሉ የሚረዳን የእግዚአብሔር ፀጋ ሁላችንንም ይርዳን አሜን።

የማንቂያ ደውል (wake up call)

የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው።         
                                                           ሮሜ 6፥23
ኩነኔ የለበት በክርስቶስ ላለ
እዳው በአንዱ ጌታ ስለተከፈለ
በፅድቅ ልንኖር ለኋጢአት ሞተናል
ማህተሙን ይዘን ማንስ ይከሰናል
የበጉ ደም ነክቶን ማን ይቋቋመናል።

ሌላ አንድ የለም


ዶሮ ታርዳ በብልት በብልት አስራ ሁለታ ቦታ ከመገነጣጠሏ በፊት አንድ ዶሮ ተብላ እንደምትጠራ ሁሉ የዚህ ፅሁፍ ርዕስም  አንድ ራሱን የቻለ መልእክት ያለው ሲሆን እንደ ዶሮ ብልት ስንገነጣጥለው ሶስት ራሳቸውን የቻሉ ወሳኝና ቆራጥ መልእክት አዘል ያነገቡ ርዕሶች ይወጡታል።  እነሱም
ሌላ     \
አንድ     }   አትኩሮት የሚሹ ወሳኝ ጉዳዮች
የለም   /

ሌላ

ሌላ የሚለው ቃል በአብዛኛው የሚያተኩረው አማራጭ ስለሆነ ጉዳይ ነው። '' ሌላ '' ያለበት ዐረፍተ ነገር የአንድን ድርጊት ውስንነት ወይም ገደብ የለሽነት በጉልህ የሚያሳይ ቁርጥ ያለ ውሳኔን ያመለክታል። ለምሳሌ ያህል ሰይጣን ''ሌላ'' በሚለው ቃል መፅሐፍ ቅዱስ ሲገልፀው  እንዲህ ይላል

ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤
                                                            ዮሐ 10:፥10

በዚህ ቃል ውስጥ የሰይጣን ዓላም በግልጽ ተቀምጧል። ሰይጣን በእኛ ላይ ከዚህ ውጪ ምንም ዓይነት ተልዕኮ የለውም። ሊያጫውትህ፣ ሊያዝናናህ፣ ሊያዳብርህ፣ ወይም በሕይወትህ የምትፈልገውን ሊሰጥህ አይመጣም። እሱ ሌባ ነው ይሰርቃል፣ ያርዳል፣ ያጠፋል ሌላ ተግባርም ሆነ ምግባር የለውም። ስለ ሰይጣን ከዚህ ውጪ የተረዳ ሰው ካለ '' ሌላ '' የሚለው ወሳኝ ቃል አመለካከቱን ቆርጦ ይጥለዋል ምክንያቱም የጌታ ቃል እጅግ ግልፅ በሆነ መልኩ ተናግሯልና።

ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በተመለከተ '' ሌላ '' በሚለው ቃል ጋር አያይዞ ከብዙ በጥቂቱ በእንዲህ ይገልፀዋል።

መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና።
                                                                 ሐዋ 4፥12
እዚህ ጋር መፅሐፍ ቅዱሳችን በአፅንዎት እንደገለፀው የመዳን ብቸኛ መንገድ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በዚህ ክፍል ውስጥ ሌላን ሁለት ጊዜ ተጠቅሞበታል፣ አንድም ከኢየሱስ ውጪ የመዳን ጉዳይ ታሳቢ እንዳላይደለና በማንም ሊሆን እንደማይችል፣ አንድም ሌላ ከእርሱ ውጪ እኛ ልንጠቀምበት የሚገባ ስም እንደሌለ። በአጭሩ ከእርሱ ውጪ አዳኝ እንደሌለ '' ሌላ '' የሚለው ቃል ይገልፅልናል። ኢየሱስ ክርስቶስ አማራጭ የሌለው ብቸኛ ምርጫ ነው። አዎ ኢየሱስ ብቸኛ አዳኝ፣ ኢየሱስ ብቸኛ ቤዛ ነው።

ከተመሠረተው በቀር ማንም ሌላ መሠረት ሊመሠርት አይችልምና፥ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።
                                                              1ኛ ቆሮ 3:፥11
ማብራራት በማይጠይቅ ሁኔታ እዚህ ጋርም መፅሐፍ ቅዱሳችን '' ሌላ '' በሚል ቃል አዘል ኢየሱስን ምርጫ የለሽ ብቸኛ ጉዳያችን እንደሆነ ዳግም በአትኩሮት ገልፆታል።

ታዲያ ከእኛ ምን ይጠበቃል? መፅሐፉ ስለእኛም '' ሌላን '' ተጠቅሞ እንዲህ ይለናል

እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ወደ በጎች በረት በበሩ የማይገባ በሌላ መንገድ ግን የሚወጣ እርሱ ሌባ ወንበዴም ነው፤
                                                                   ዮሐ 10፥1
ኢየሱስ ራሱን ብቸኛ ከሰማይ የመጣ እውነተኛ መንገድ መሆኑን በተለያየ ምሳሌዎች ነግሮናል። ለዚህም እርሱን ብቻ መንገድ አርገን ሕይወታችንን ማቅናት አለብን። በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም ብሎናል። ከእርሱ ውጪ መንገድ አደላድለን ከሆነ መንገዳችንን ማቅናት ይኖርብናል። ወንበዴነታችንን ወደነው ካልሆነ በቀር ብቸኛ መንገዳችን የቃሉ ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

'' ሌላ '' የሚለው ቃል ከኢየሱስ ውጪ እንዳናይ፣ እንዳናስብ፣ እንዳንመለከት፣ እንዳንሻም ያሳስባል።

አንድ
በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ቁጥርን ወይም ብዛት ለማመልከት ከተጠቀሰበት ዓላማ ውጪ መንገድን፣ ሁኔታን፣ ትዕዛዝን፣ ፍቃድን ወይም የእግዚአብሔር ሀሳብ በግልፅ ከማስቀመጥ አንፃር '' አንድ '' ተብሎ በተነገረባቸው ቦታዎች ሁሉ እግዚአብሔር በቃሉ ምን ያህል ሊያሳስበን እንደፈለገ በቀላሉ መረዳት እንችላለን። አንድ የሚለው ቃል የሚያሳየው ከምርጫ ውጪ የሆነን ነገር በብቸኛነት የሚያጠቁም ወይም የሚያሳይ ወሳኝ ቃል ነው።

ይህ ''አንድ'' የሚለው ቃል በሕይወታችን ውስጥ ትርጉም የሚሰጥና ከእግዚአብሔር ሀሳብ ጋር የሚያግባባን መሰረታዊ ቃል ነው። መፅሐፍ እንደሚል በአንዱ መተላለፍ ኋጢአት በሰው ልጆች ሁሉ ላይ ነገሰ ሞትንም አስከተለ ነገር ግን በአንዱ በኢየሱስ መታዘዝ ሕይወት ሆነልን (ሮሜ 5፥12-17)።

ሰው ከኋጢአትና ከዘላለም ሞት እንዲድን እግዚአብሔር ያዘጋጀው የመዳን መንገድ አንድ ልጁ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው እንደ ዮሐንስ ወንጌል 14፥6 መሰረት። በሌላ በኩል

ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው፤
                                                       1ኛ ጢሞ 1፥15

ከዚህ የምንረዳው ማንም ከኢየሱስ በቀር የእኛን ኋጢአት ሊያስቀር ወደዚህ ዓለም የመጣ እንደሌለ ነው። የዓለምን ኋጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ ተገለጠ የተባለለት እርሱ ብቻ ነው። ለዚህም በተደጋጋሚ ክርስቶስን በብቸኛነት '' አንድ '' በማለት ይገልፀዋል። ለምሳሌ ያህል:-

=}} አንዱ ስለ ሁሉ ሞተ (2ኛቆሮ 5፥14)
=}} ነፍሱን ለብዙዎች ቤዛ ሰጠ (ማር 10፥45/1ኛ ጢሞ 2፥6)

መፅሐፍ ቅዱሳችን '' አንድ '' ሲል ሌላ እንደሌለ ልንረዳ ይገባል። እኛን በተመለከተ የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ይላል

ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፤ አስተዋይም የለም፤ እግዚአብሔርንም የሚፈልግ የለም፤ ሁሉ ተሳስተዋል፥
                                                             ሮሜ 3:፥11

 ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል፤
                                                              ሮሜ 3፥23

ሁሉ የሚለው ቃል ውስጥ አንድ እንኳ መምዘዝ አንችልም መፅሐፉ በድግግሞሽ በማሳሰብ ዘግቶታል። ሁሉም የሰው ዘር በሙሉ በክርስቶስ ኢየሱስ ክቡር ደም መቤዥት አስፈልጎታል። ከእግዚአብሔር ክብር ጎድለን የነበርነውን እርሱ መልሶልናል። ከኋጢአት በቀር በነገር ሁሉ እኛን የመሰለው ጌታችን ኢየሱስ በመካል የነበረውን የጥል ግድግዳ ያፈረሰ እርሱ ብቻ ነው። ይህንንም መፅሐፍ ሲናገር

አንድ እግዚአብሔር አለና፥ በእግዚአብሔርና በሰውም መካከል ያለው መካከለኛው ደግሞ አንድ አለ፥ እርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤
                                                           1ኛ ጢሞ 2፥5
ቃሉ በአፅንሆት እንደገለፀው በመካከል ያለው አንድ ብቻ ነው እዚህ መካከለኛ ላይ መጨመርም ሆነ ከተጠቀሰው መካከለኛ ሌላ መፈለግ አይቻልም። ሰው ያሻውን ይጨምር ይሆናል በእግዚብሔር ዘንድ ግን ተቀባይነት የለውም።

አንድ ጌታ ኢየሱስ አለኝ ክርስቶስ አለኝ
ነፍሴን ነፍሱ ያደረገልኝ የሚዋጋልኝ
ማይፈታ ምይተሜ ነው ደሙ
ከፍ ላርገው አርማዬ ነው ስሙ

የለም
ይህ ቃል በአጭሩ የሚያስረዳው ከላይ ካየናቸው ሁለት ወሳኝ ጉዳዮች ውጪ ሌላ እንደሌለ ነው። አዎ ሌላ አንድ የለም። መፅሐፉ ካስቀመጠልን መዳኛ ውጪ ሌላ አንድስ እንኳ የለም። ትርፉ ጉንጭ ማልፋት እንጂ ።

መዳን ከኢየሱስ ውጪ በሌላ በአንድስ እንኳ የለም (ሐዋ 4፥12)። እርሱ ብቸኛ መዳኛ ነው። ከእርሱ ሌላ አምባ የለም ማንም የለም ማንንም አላውቅም ይላል እግዚአብሔር እኛስ?

እኔ በበኩላ
የለም ሌላ ስም ሌላ መዳኝ
ከሰማይ በታች መተማመኛ

ከቤዛዬ፣ በድካሜ ከሚራራልኝ ሊቀካህኔ፣ ደሙ ዘላለም ከሚያነፃ ከኢየሱስ ውጪ ሌላ አንድ የለም ብያለው። እናንተስ?

እግዚአብሔር ሁሌም መልካም ነው

በመልካም ሁኔታ ውስጥ ሆነን እግዚአብሔርን ማመስገን ተለማምደን ይሆናል ችግር ወይም መከራ ውስጥ ገብተን ግን ብዙ ጊዜ ማመስገን ይከብደናል። ችግር ወይም መከራ የእግዚአብሔርን መልካምነት አያጎድልም። እርሱ ሁልጊዜ ከመልካምነት አይጎድልም ስሙ ብሩክ ይሁን።

እግዚአብሔር በእምነት እንድናድግ በፈተና ውስጥ ያሳልፈናል። እምነት ደግሞ ካልተፈተነ ብርታቱ ወይም ጥንካሬው አይታወቅም። ወርቅ በእሳት ካልተፈተነ እንዲል መፅሐፍ ቅዱሳችን የሰው ልጅም እንዲሁ ነው። እርሱ በትንሹ ሲፈትነን ለትልቁ እያዘጋጀን እንደሆነ መዘንጋት የለብንም። በፈተና ውስጥ በእምነት እንድናድግ እንጂ እንድንወድቅ ከቶ አይፈልግም። ይልቁንስ በእርሱ አብልጠን እንድንደገፍ ወይም እንድናምን በፈተና ውስጥ ያስተምረናል።

ታዲያ እግዚአብሔር እኛን እየፈተነ ባለበት ሁኔት ውስጥ ሆነን መልካሙነቱ መናገር የምንችልበት እምነት አለን ወይ? ብለን ራሳችንን መጠየቅ ብልህነት ነው። ይህን ካደረግን በእውነት እግዚአብሔር በእኛ ላይ ያለው ዓላማ እውን ሆኗል ማለት ነው።

ኢዮብ የነበረውን አጥቶ፣ ጤናው ተቃውሶ ሰውነቱ በቁስል ሲወረር ሚስቱ እግዚአብሔርን እርገምና ሙት ባለችው ጊዜ የመለሰው መልስ ለእግዚአብሔር የሚገባው ምስጋና ነበር።

ከእግዚአብሔር እጅ መልካሙን ተቀበልን፥ ክፉ ነገርንስ አንቀበልምን? አላት። በዚህ ሁሉ ኢዮብ በከንፈሩ አልበደለም።     
                                                          ኢዮ 2፥10

አዎ ብዙ መልካም ነገሮች ተቀብለን በአንድ ትንሽ ጊዜአዊ ችግር ምክንያት እግዚአብሔርን ከማማረር የሚጠብቅ የእርሱ ጸጋ ሁላችንንም ይርዳ። በተሰጠን በረከት ላይ ሳይሆን በበረከቱ አምላክ ላይ ልበ ሙሉ እምነት ይኑረን። ኢዮብ የነበረውን ሳይሆን ሰጪውን አሻግሮ ተመልክቷል። እምነቱም በእርሱ ላይ ብቻ ነበረ። በነዛ ሁሉ ችግሮች ውስጥ ሆኖ እንኳ እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔር ነሳ የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን ነው ያለው። በችግር ውስጥ ሆኖ ባረከ። ኢዮብ በችግሩ ኋይለኛነት ሳይሆን እምነቱን ባሳረፈበት አምላክ ኋይል ተማርኳል። አንድ ደስ የሚለኝ አባባል አለ:-

'' ለእግዚአብሔር የችግርህን ታላቅነት አትንገር
ለችግርህ የእግዚአብሔርን ታላቅነት ንገረው ''

እግዚአብሔር ሲሰጥም ሲነፍግም ትክክል ነው መልካምም ነው። የማይጠቅመንን ነገር በመከልከል ይጠብቀናል የሚያስፈልገንን ነገር ሳንነግረው የሚያውቅ እርሱ በራሱ የጊዜ ሰሌዳ ያከናውንልናል ይሰጠንማል። አዎ እግዚአብሔር መልካም ነው።

ችግርን ለጥቅማችን ያመጣዋል ከችግር መውጫንም እርሱ ያዘጋል እግዚአብሔር እጅግ መልካም ነው።

የሚበልጥ ፍቅር

'' እምነት ተስፋ ፍቅር እነዚህ ሦስቱ ጸንተው ይኖራሉ፤ ከእነዚህም የሚበልጠው ፍቅር ነው።"  (1ኛ ቆሮ13፥13)

ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ለዘመናት ብዙ ተብሏል ግን ፍቅሩ ሳይበርድ ዛሬም ትኩስ እንደሆነና በሕይወታችንም ሲሰራ እያየነው እንገኛለን። እግዚአብሔር በባህሪው አፍቃሪ አምላክ ነው። ለመፈጠራችን፣ ደግሞት በኋጢአት ወድቀን ሳለ በበደላችን ሙታን በሆን ግዜ ከልጁ ጋር ሕይወት የሰጠን (ለደህንነታችን) መሰረት የእርሱ ፍቅር ነው።

በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።
                                                    ዮሐ 3፥16

ከፍቅሩ ብዛት እንዲሁ የወደደን እግዚአብሔር ስሙ ብሩክ ይሁን። ከእኛ ምንም ሳይጠብቅ እንዲሁ የፈለገን አንድ ልጁን በመስጠት ፍቅሩን የገለፀ መልካም የፍቅር አባት ነው። ይህ ፍቅር ነው ታሪካችንን ቀይሮ ወደ ገዛ ፍቅሩ ልጅ መንግስት ያፈለሰን።

በየዘመናቱ ይህ ፍቅር ተሰብኳል፣ ከፀሐይ መውጫ እስከ መጥለቂያ ላለው የሰው ዘር በሙሉ ምስራች ተነግሯል ነገር ግን እንደ እግዚአብሔር የዘላለም ሀሳቡን እንደ ልቡ ምክር በፍቅር ልንኖር አቅቶናል። እኛ ቤተሰቦቻችንን፣ ወዳጆቻችንና ወገኖችንን የምናፈቅረው ከእግዚአብሔር አምሳል ስተለቀዳን ነው። ግን የእርሱ ፍቅር ፍፁም ሙሉ የእኛ ግን ጎዶሎ ነው። ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ በደልና ኋጢአት በመስቀል ላይ ሲሰቀል እኛ ግን የገዛ ጥፋታችንን ማመን ተስኖናል። እርሱ ለሰቃዮቹ ይቅርታና ምህረት ሲለምን እኛ ግን ወዳጆቻችንን እንኳ በቅጡ መውደድ አቅቶናል።

ዓለምን ብንዞር ብንዞር ለበደለ ባሪያ አይደለም ለጨዋ ባሪያ ልጁን የሚሰጥ አናገኝም። ለዚህም ነው ሐዋርያው ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ 5፥6-11 በዝርዝር ያስረዳው።

የሰው ፍቅር እስከ መቃብር ነው። አብዛኛው ኢትዮጵያዊ '' ፍቅር እስከ መቃብር '' የሚለውን መፅሐፍ ያውቀዋል። አዎ የሰው ፍቅር የተገደበ ነው። የእርሱ ፍቅር ግን ወሰን የለውም። እርሱ ፍቅር ነውና። በልጁ የገለጠው ፍቅር የመውደድ ጥግ ነው። የፍቅር ዳርቻ እርሱ እግዚአብሔር ነው።

አቤልና ቃየንን መመልከት እንችላለን። ለሁለቱም መስዋህት የማቅረብ የተሰጠው ጥያቄ አንድ ነው። ነገር ጥያቄውን የመፈፀም ልዩነት ግን አለ። በዘፍጥረት ምዕራፍ አራት ከቁጥር አራት ጀምረን ብናነብ አቤል የቃየን መስዋህት ተቀባይነት እንዳያገኝ ምንም አላደረገም። እርሱ የራሱን ብቻ ነው ያቀረበው። የቃየንን አልተቸም ወይም የወንድሙን ልብ አላሸፈተም። ፍቅር በሚጠይቀው መልኩ አቀረበ እግዚአብሔርም መስዋቱን ተቀበለው።

በአንፃሩ ቃየንን ስናየው ፍቅር ከማጣቱ የተነሳ በወንድሙ ላይ እንዲነሳሳ አደረገው። መስዋቱን ያልተቀበለው እግዚአብሔር ሆኖ ሳለ ነገር ግን እጁ የሌለበትን ወንድሙን ሲገድል እናነባለን። ከወንድሙ ሊማር ሲገባ የእሱ ድካም ምንጭ ወንድሙ አድርጎ ስለቆጠረ ተበቀለው። ነገር ግን አቤል ባይኖር እንኳ እግዚአብሔር የቃየንን መስዋህት አይቀበልም ነበር። የእግዚአብሔር በር ሁሌም ክፍት ነው። ቃየን ራሱን ለውጦ ዳግም መስዋህት ማቅረብ ይችል ነበር።

የሰዉ በር ቋሚ አይደለም ካሻን እንከፍታለን ካሻን ደግሞ ዘግተን በራሳችን አጥር እንኖራለን። የእግዚአብሔር ቋሚና ዘላቂ ነው የእኛ ግን በሁኔታዎች የተከበበ ነው። በሕይወታችን የብዙ ሰዎች በር ተዘግቶብናል የእርሱ ግን ላይዘጋ የተከፈተ ነው።  በወዳጆቻችን ውንጀላ ተሰላችተናል እርሱ ግን በውድ ደሙ ነጠብጣብ አፈቅራችኋለው የሚል አፍቃሪ ነው ስሙ ይቀደስ።

እግዚአብሔር በምን ያህል የፍቅር መጠን እንደወደደን ነግሮናል

እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ፤ እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፥ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ፥ የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ፤ እንዲሁም ዓለም አንተ እንደ ላክኸኝ በወደድኸኝም መጠን እነርሱን እንደ ወደድሃቸው ያውቃል።
                                                        ዮሐ 17፥22-23

 እኛስ ምን ያህል እንወደዋለን? እርስ በራሳችን ምን ያህል እንዋደዳለን?

እኛ ፍቅራችንን ስንገልጥ ምናልባት የዓባይ ወንዝን ርዝመት የሚያህል ወይም የኪሊማንጃሮ ተራራን ከፍታ የሚያህል ልንል እንችላለን እርሱ ግን አንድያ ልጁን የናዝሬቱ ኢየሱስን በወደደበት መጠን ወዶናል። ታዲያ አፍቃሪ ፍቅር ይፈልጋል። የሰጠንን ስንኖረው ማየት ይሻል በወንድማማች መዋደድ  ተመላለሱም ተብሎ እንደተፃፈ አንደ ቃሉ እንድንኖር የጌታ ፀጋ ይርዳን።

ፍቅር የሆነው እርሱ ኢየሱስ በፍቅር ዋጋ ገዝቶናል። አንድ መቶ ብር  የሚያወጣ እቃ ስትገዙ መቼም አንድ ሺህ ብር ቀብድ አትከፍሉበትም። እርሱ ግን ኋጢአት የሚጠይቀውን ሁሉ ቅጣተ ለነበረው ለአሁኑም ወደ ፊትም ለሚደረጉ አመፃዎች ኢየሱስ በፍቅር ከፍሏል። እንደተከፈለልን ዋጋ መኖር ይሁንልን።

ምክር
1) ወንድሞች ሆይ፥ እናንተ ለአርነት ተጠርታችኋልና፤ ብቻ አርነታችሁ ለሥጋ ምክንያትን አይስጥ፥ ነገር ግን በፍቅር እርስ በርሳችሁ እንደ ባሪያዎች ሁኑ።
                                                    ገላ 5፥13
2) በትሕትና ሁሉና በየዋህነት በትዕግሥትም፤ እርስ በርሳችሁ በፍቅር ታገሡ
                                                     ኤፌ 4:፥2
3) ነገር ግን እውነትን በፍቅር እየያዝን በነገር ሁሉ ወደ እርሱ ራስ ወደሚሆን ወደ ክርስቶስ እንደግ
                                                     ኤፌ4፥15

4) ክርስቶስም ደግሞ እንደ ወደዳችሁ ለእግዚአብሔርም የመዓዛ ሽታ የሚሆንን መባንና መሥዋዕትን አድርጎ ስለ እናንተ ራሱን አሳልፎ እንደ ሰጠ በፍቅር ተመላለሱ።
                                                     ኤፌ 5፥2

5) ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል እንጂ በፍቅር ፍርሃት የለም፥ ፍርሃት ቅጣት አለውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም።
                                                     1ኛ ዮሐ4፥18

6) በእናንተ ዘንድ ሁሉ በፍቅር ይሁን።
                                                   1ኛ ቆሮ 16፥14

7) በፍቅር አሳሳም እርስ በርሳችሁ ሰላምታ ተሰጣጡ። በክርስቶስ ላላችሁ ለሁላችሁ ሰላም ይሁን። አሜን።
                                                 1ኛ ጴጥ 5፥14