እግዚአብሔር እኛን ከፈጠረበት አንዱ ምክንያት ከእርሱ ጋር ህብረት እንድናደርግ ነው። ለዚህም ነው '' በመልካችን እንደ ምሳሌአችን '' እንፍጠር (ዘፍ 1፥26) ያለው። ከእርሱ ጋር ብቻ ሳይሆን ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድም መልካም እንዳልሆነ በመናገር አጋር እንደሚያስፈልገው ስላወቀ የሚመቸውን ረዳት ፈጠረለት። ሰው ብቸኛ መሆን እንደሌለበት ከፍጥረቱ መረዳት ይቻላል።
በመፅሐፍ እንደምናነበው ሰው ብቻውን ሲሆን መልካም ያልነው በኅብረት ሲሆን ደግሞ በዛው ልክ መልካምና ያማረ ነው። እንዲህ ተብሎም እንደተፃፈ
'' ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ፥ እነሆ፥ መልካም ነው፥ እነሆም፥ ያማረ ነው። ከራስ እስከ ጢም እንደሚፈስስ፥ እስከ አሮን ጢም፥ በልብሱ መደረቢያ እንደሚወርድ ሽቱ ነው። በጽዮን ተራሮች እንደሚወርድ እንደ አርሞንዔም ጠል ነው፤ በዚያ እግዚአብሔር በረከቱን ሕይወትንም እስከ ዘላለም አዝዞአልና። '' (መዝ 133፥1-3)
አሮን በበረሃ ጉዞ ላይ በሊቀካህንነት ሲሾም የበረሀው ንዳድ ያደረቀውን በራሱ ላይ የፈሰሰው ዘይት ራሱን እንዳረሰረሰው መልካም፣ በበረሀ ያለው አድካሚ ጉዞ አልቦ የሰውነትን ጠረን እንደሚቀየር በልብሰ ተክህኖውም ላይ ያማረ ልዩና ጥሩ መአዛ ያለው ሽቱ እንደተረጨው መልካም፣ የበረሀ ንዳዱ ከፍተኛ የውሃ ጥምን ባመጣ ጊዜ ከበረዶሃማ ተራራ ጫፍ ላይ ጥምን የሚያረካ ቀዝቃዛ ውሃ እንደሚወርድ መልካም የወንድሞ በህብረት መሆን እጅግ መልካም ነው።
በሌሎች መሰብሰብ ውስጥ የማይገኝ በዚህ በወንድሞች በኅብረት መቀመጥ ብቻ ለዘላለም የታዘዘ በረከትና ሕይወት እግዚአብሔር አዟል። ይህ ደግሞ እንዴት ያለ መልካም ነገር መሆኑ ይበልጥ ያሰረዳል።
እንደ ልቡ ሀሳብና ምክር መቀመጥ ይሁንልን።
ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ፥ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና፥ ኤፌ 2፥4-5
Monday, 30 December 2019
የመንገድ ላይ መድሃኒት
ኢየሱስ የሚለው ስም በየመንገዱ ሲጠራ ደስ የማይላቸው ብዙ ሰዎች እንዳሉ መናገር የሚከብድ ነገር አይደለም። በአብዛኛው ሰዎች ሞቅ ባለ ጨዋታቸው ይሁን በስራ ጊዜአቸው ሊሰሙት የማይፈልጉት ስም ጥራ ብትሉኝ ይህን ስም ብቻ ነው።
በሀገራችን በተለያዩ ስፍራዎች ከወዳጆቻችን ጋር ተሰብስበን የማውራት ልማድ አለን። በእነዚህ መሰል ጊዜአት የማይነሳ ርዕሰ ጉዳይ አይኖርም ብንል ማጋነን አይሆንም። ፖለቲካ ቢሉ ሃይማኖት፣ ቅልድ ቢሉ ፌዝ፣ የስራ መቀዝቀዝ ቢሉ የኑሮ ውድነት፣ ሽንኩርት ቢሉ ዘይት፣ ዘፋኝ ቢሉ ተዋናይ፣ ደራሲ ቢሉ ፈላስፋ፣ ሜሲ ቢሉ ሮናልዶ፣ አርሴናል ቢሉ ማንቼ፣ ሀይሌ ቢሉ ደራርቱ፣ የሃይማኖት አባት ቢሉ ሰይጣን ጭምር ብዙ አልባሌ ነገሮች............ ብቻ የማይወራ የለም። ሁሉም ጫወታ ይወዳል ጆሮውን ቀስሮ ያዳምጣል የሚያስቅ ያስቀዋል።
በዚህ መሀል ድንገት ስለ ኢየሱስ ከተነሳ ወይም አንድ ሰው በአቅራቢያ ሆኖ ይህን ስም እየጠራ ሰዎች ወደ እግዚብሔር እንዲቀርቡ የማንቂያ ደውል ለማሰማት ከመጽሐፍ ቅዱስ እየጠቀሰ ብቸኛ አዳኝነቱን (መድሃኒትነቱን)፣ እውነተኝነቱን፣ መንገድነቱን፣ ተስፋነቱን፣ አጽናኝነቱን መናገር ሲጀምር አታስዋሹኝ ብዙ ፊቶች መቀያየር ይጀምራሉ። ከፊል ፊቶች እንደ ቲማቲም ይቀላሉ ከፊሉ ደግሞ ጥርሱን ያፏጫል አንዳንዱም ሊማታ ይዳዳውል።
ስለቀልድና ዋዛ ፈዛዛው ቦታ ሳይመርጥ ሲያውካካና ሲያሽካካ የነበረ ስለ ኢየሱስ መስማት ቦታ ያጡና '' ወንጌል ቦታ አለው '' በማለት ይደነፋሉ። ጭራሽ ጫወታችንን አታበላሽ ብለው የሚያጉረመርሙም አይጠፉም። ስለፖለቲካ ፣ ፌዝ፣ እርባና ስለሌለው ቀልድና ስለብልግና ማውራት እንደጥሩ ጫወታ ተቆጥሮ ስለ ኢየሱስ መስማት ግን ጫወታን እንደማበላሸት ሆኖ የሚቆጠርባቸው ጊዜአት ብዙ ናቸው።
ዘፈንና ቀልዱ፣ ቧልትና ፌዙ ሲነገር ሁሉ ያለምንም ልዩነት አንድ ሆነው ሲስቁና ሲፈነድቁ እንዳልነበር '' ኢየሱስ '' የሚለው ስም ሲጠራ የሚበሳጩበት ምክንያት ምንድነው? ዛሬም ድረስ የሚያሳዝነኝ ጥያቄ ነው። ስለ ምድራዊ ነገር ማውራት ለሁሉም የተፈቀ ተግባር ለሰው ልጆች ሁሉ ስለሞተው ስለ ኢየሱስ ብቸኛ መድሃኒትነት መናገር ደግሞ ለተወሰኑ ሰዎች ብቻ የተሰጠ ስጦታ ሆኖ መመስከርን የሚያስወቅስ ተግባር ሆኖ የሚቆጠርበት ምክንያት መኖር ይበልጥ ያሳዝነኛል። በምድራዊ ጉዳይ ሽንጡን ገትሮ የሚከራከር ስለ ኢየሱስ ሲሆን ግን ራሱን ያገላል።
ብዙ ኢትዮጵያዊያን ወንጌል በመንገድ ተመስክሮልን እንደተቀበልነው ይስማማሉ ነገር ግን በመንገድ ላይ ከተነገረን ወንጌል ይልቅ ወንጌሉን ስለ ተቀበለው ሰው ማቀንቀን ይቀናናል። ስለ ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ በስፋት ይነገራል ግን እንዴት ባለ ሁኔታ እንደተቀበለው ልብ የሚል አናሳ ነው። ኢትዮያዊው ጃንደረባ ፊልጶስ ስለ ኢየሱስ በመንገድ ከሰበከለት በኃላ የነበረው ምላሽ ሁለት ነው ጥምቀትን መሻቱና በልቡ ደስ ተሰኝቶ መመለሱ እንጂ ስፍራው አይደለም፣ የእናትና አባቴን ሃይማኖቴ ተከትዬ ከኢትዮጵያ ኢየሩሳሌም ድረስ ለስግደት ያስመጣኝን፣ ተራራ የወጣሁበትን፣ ዳገት ቁልቁለቱን የወረድኩበትን፣ ወንዝ የተሻገርከበትን፣ ይህን ምድር የረገጥኩበትን፣ ታላቅ የበረከት ጉዞ አድርጌ ከመመለስ ባለፈ የእናንተን ኢየሱስን ለመስማት አልመጣሁም ብሎ ፊት አልነሳም። ይልቅስ ለመስማት እጅጉን ጓጓ።
ስለ ኢየሱስ መስማት ደስ የሚያሰኝ እንጂ የሚያስኮርፍም የሚያሳፍርም አይደለም። በመፅሐፍ እንደተፃፈ የኤማሁስ መንገደኞችን ብንመለከት ስለ ኢየሱስ ሲሰሙ የተሰማቸውን እኛም በዘመናችን ሊሰማን ያስፈልጋል።
" እርስ በርሳቸውም። በመንገድ ሲናገረን መጻሕፍትንም ሲከፍትልን ልባችን ይቃጠልብን አልነበረምን? ተባባሉ። "
(የሉቃስ ወንጌል 24: 32)
ከጥቂት ጊዜአት ጀምሮ ብዙ ሰው በሚያልፍባቸው ስፍራዎች በተለይ በገበያ አካቢዎች ቀልቤን የሳበው ነገር ቢኖር '' ዘራ መድሃኒት '' እየተባለ ስለሚሸጠው የአይጥና የበረሮ መርዝ ነው። የዚህ መድሃኒት ማስታወቂያን ልብ ብላችሁ ካዳመጣችሁት '' ታላቅ የምስራች '' ብሎ ነው የሚጀምረው እውነት የቱ መድሃኒት ነው ታላቅ የምስራች?
የማያናድደው? ቦታ ማይገድበው? የማያበሳጨው? የማያስቆጣው?
እኔ እያወራውት ያለሁት ከኃጢአት የሚያድን እርሱን ብቻ በማመን የዘላለም ሕይወት ስለሚያስገኘው ኢየሱስ ነው። ስለ ዘራ መድሃኒት ሲሰማ ያልተሸማቀቀው ጆሮ ኢየሱስ ስለሚባለው መድሃኒት ጆሮውን የሚያከው ለምንደነው? እስኪ መልሱልኝ?
የሰማይ ማስተዋል በኢየሱስ ለኢትዮጵያዊያን ይብዛ አሜን።
Thursday, 19 December 2019
የፍቅር ሽፋኑ
ለሰው ልጅ ለኑሮው እጅግ በጣም አስፈላጊ ነገሮች ውስጥ በዋነኛነት ከሚጠቀሱት ውስጥ ልብስና መጠለያ ናቸው። ሁለቱም የሰውን ልጅ ከተፈጥሮና ከእይታ የሚከልሉ ወሳኝ ነገሮች ናቸው። እንደው በአጠቃላይ እኛ ሰዎች ስንባል፤ ካልተሸፈንን መኖር እንደማንችል ከሚያስፈልገን ነገሮች መረዳት እንችላልን። ህልውናችንም የሚቀጥለው በመሸፈን ውስጥ ነው ብንል ይቀላል። ማንም ከእንቅልፉ እንደተነሳ ራቁቱን ወደ ውጭ አይወጣም ወይም መሸብኝ ብሎ መንገድ ዳር አይተኛም።
የመጀመሪያ ፍጥረታት የሆኑት አዳምና ሄዋን ከተላለፉ በኃላ በመጀመሪያ ያደረጉት ነገር ቢኖር ራሳቸውን መሸፈን ነበር። በበለስ ቅጠል ግልድም አሰሩ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በዘመናችን ጅንስ እስከምንለው ድረስ ሁሉም ሰውነቱን በመሸፈን ይኖራል። እግዚአብሔር ግን መልካም ነውና የሰው ልጅ ያገለደመው ቅጠል ቶሎ የሚደርቅ በመሆኑ የልጁን መሰዋት ምሳሌ በማድረግ ዘላቂውን ቁርበት አለበሳቸው።
ይህ በሥጋ መሸፈን ዛሬም የሚያስፈልግ ቢሆንም እንኳ አዳምና ሄዋን ያደረጉት ቅጠል የሰውን ጽድቅ ያሳያል። እንደ ጠዋት ጤዛ ታይቶ የሚጠፋ፣ በቶሎ የሚደርቅ፣ አለ ሲባል የሌለ ነው። ሁሉቱም ይህን ሲያደርጉ መንፈሳዊ ስሌት የሌለበት ሥጋን ብቻ ያተኮረ መፍትሄ ነበር የወሰዱት እግዚአብሔር ግን ጉዳዩን ቀየረው እንጂ። ቁርበት የእግዚአሔርን ጽድቅ ሲወክል ዘላቂነትንም የሚያሳይና መሸፈን ለሚያስፈልገው ማንነት በመስዋህትነት የሚቀርብ ሥጦታ እንደሆነ መረዳት እንችላልን።
ከብሉይ ኪዳን የጽድቅ ስራዎች ተብለው ከሚዘረዘሩት ውስጥ አንዱ ማጋለጥ ነው። ሕጉ በሚያዘው መጠን መጋለጥ ያለበት ነገር፣ መውጣት ያለበት፣ መነገር ያለበት ወሬ ያለ ርእራሄ እስከ ሞት ድረስ እንኳ ዋጋ ቢያስከፍል ጉዳዩ ለእስራኤል ሕዝብ ይጋለጣል። እንዲህ ተብሎ እንደተፃፈ ማንም ሌሎች አማልክት እናምልክ ብሎ ቢያስትህ፥ እሺ አትበለው፥ አትስማውም፤ ዓይንህም አይራራለት፥ አትማረውም፥ አትሸሽገውም፤ ነገር ግን ፈጽመህ ግደለው፤ (ዘዳ 13፥6-10)
ለአብነት ያህል ሌላ ከዚሁ ከዘዳግም መፅሐፍ አንድ ምሳሌ እንውሰድ:-
ማንም ሰው ለአባቱ ቃልና ለእናቱ ቃል የማይታዘዝ ቢቀጡትም የማይሰማቸው እልከኛና ዓመፀኛ ልጅ ቢኖረው፥ አባቱና እናቱ ይዘው ወደ ከተማው ሽማግሌዎች ወደሚኖሩበትም ስፍራ በር ያምጡት፤ የከተማውንም ሽማግሌዎች። ይህ ልጃችን እልከኛና ዓመፀኛ ነው፥ ለቃላችንም አይታዘዝም ስስታምና ሰካራም ነው ይበሉአቸው። የከተማውም ሰዎች ሁሉ እስኪሞት ድረስ በድንጋይ ይውገሩት፤ እንዲህም ክፉውን ነገር ከመካከልህ ታርቃለህ፥ እስራኤልም ሁሉ ሰምተው ይፈራሉ። (ዘዳ 21፥18-21)
ሕጉ የሚያሳየው ምን ያህል ማጋለጥ ዋጋ ያለው ነገር እንደሆነ ነው። ወላጆች ልጆቻቸውን እንኳ ለሞት አሳልፈው እስኪሰጡ ድረስ የሚያሰጨክን የማጋለጥ ስራ የታዘዙበት ሕግ ነው። ነገር ግን ማጋለጥ ብቻ እውነት አይደለም ይልቁንስ መሸፈን በሙላት የሚሰራ እግዚአብሔር ያዘጋጀው የአዲስ ኪዳን ጽድቅ ነው። አዳምንና ሄዋንን በቁርበት የሸፈነው እርሱ የዓለምን ኃጢአት ሁሉ ውድ ልጁን ኢየሱስን በመስጠት ከድኖታል።
መፅሐፍ እንደሚል "፤ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና። " (ዮሐ 3፥16) ይህ መውደድ ነው የዓለም ኃጢአት የሸፈነው። የሰው ልጅ የኃጢአቱ ብዛት ግንባሩ ላይ ቢፃፍ አይደለም ከእግዚአብሔር ፊት ሊቆም፤ እርስ በራሳችን እንኳ ለመተያየት ባልደፈርን ነበር። መወደድ ያመጣው መሸፈን ማለት ይህ ነው። እግዚአብሔር ስሙ ይባረክ በባሕሪው ሸፋኝ ነው። እንዲህ ተብሎ እንደተፃፈ " የእግዚአብሔር ክብር ነገርን መሰወር ነው፤ የነገሥታት ክብር ግን ነገርን መመርመር ነው። " (ምሳ 25፥2)
መሸፈን የኢዲስ ኪዳን ጽድቅ ነው። ክርስቲያን ከክርስቲያን ጋር በሚኖረው ግንኙነት ውስጥ አንዱ ቢበድለው በመጀመሪያ ብቻውን ያናግረው የተባለውም መሸፈን ስላለብን ነው። በማጋለጥ ውስጥ ብዙ ትርፍ አለው ለዚህም ቀዱሱ መፅሐፍ ሲመሰክር '' ወንድሞቼ ሆይ፥ ከእናንተ ማንም ከእውነት ቢስት አንዱም ቢመልሰው፥ ኃጢአተኛን ከተሳሳተበት መንገድ የሚመልሰው ነፍሱን ከሞት እንዲያድን፥ የኃጢአትንም ብዛት እንዲሸፍን ይወቅ። '' (ያዕ 5፥19-20)
ዛሬ ላይ ሰው ለሰው የማይተኛበት ዘመን ላይ ነን። በምዕራባዊያን ዘንድ እንደተለመደው የሰውን ገመና ፈልፍሎ እንደሚያወጣው ፓፓራዚ የሰውን ምስጢር መጠበቅ አቅቶን ጭራሽ ገመና ፈላጊዎች ሆነናል። ጌታ ኢየሱስ ማስተዋል ያብዛልን። ስለ ሰው ድካም መቁጠር አቁመን የተተወልልን በደላችንን እያሰብን፣ የቀረልንን ቁጣ እያሰላሰልን አመስጋኝ እንድንሆንና አንድ ሰው በድካም ውስጥ ብናየው ያ ሰው እንዲመለሰ የፀሎት ርዕስ እንዲሆነን እመክራለው።
" ትጸልዩም ዘንድ በመጠን ኑሩ፤ ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ። " (1ኛ ጴጥ 4፥8) እዚህ ላይ ማስተዋል ያለብን '' ከሁሉ በፊት '' የሚለውን ኃይለ ቃል ነው። አዎ ከምንም በፊት ፍቅር ይቀድማል። በሌላ ስፍራ እንደምናነበው ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ እንደሚል ለየትኛውም የመንፈሳዊ ሕይወት እንቅስቃሴ ይህ ፍቅር መሰረት ነው። ይህ ፍቅር ሲኖረን ነው የወዳጆቻችንን ሰንፍና የምንሸፍነው። ከላይ እንዳነበብነው ፍቅር የኃጢአትን ብዛት የመሸፈን አቅምና ጉልበት አለው። ስለተሸፈነልን እንሸፍን። በመሸፈን ውስጥ እጅግ ብዙ ትርፍ አለና።
ጌታ ኢየሱስ በቀራኒዮ መስቀል ላይ ያፈሰሰው ደም ከፍቅር የተነሳ ነው። " ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል። " (ሮሜ 5፥8) የዚህን የክርስቶስ ኢየሱስ ፍቅር ስፋቱና ርዝመቱ ከፍታውም ጥልቅነቱም ምን ያህል መሆኑን ለማስተዋል፥ ከመታወቅም የሚያልፈውን ለማወቅ እንበረቱ ዘንድ ዓለምን የሞላት የእርሱ ጸጋ ሁላችንንም ይርዳን አሜን።
በየትኛውም ስፍራ በማንኛውም ሰዓት ሁሉም ሰው ማየት ያለበት ይህን ፍቅር ነው። ዓለምን በደሙ የከደነ የኢየሱስ ደም ዛሬም ትኩስ ነው ከኃጢአት ያነፃል፣ በደልን ይሸፍናል፣ አዲስ ሰው ያደርጋል፣ ለዘላለም ያድናል።
Subscribe to:
Posts (Atom)