ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ፥ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና፥ ኤፌ 2፥4-5
Tuesday, 17 September 2019
ታላቅ መዳን
ሰው ከብዙ ነገር ሊድን ይችላል ነገር ግን በመፅሐፍ ቅዱሳችን እንደምናነበው ዘላለማዊ መዳንን የሚያክል ታላቅ መዳን የለም። ይህ መዳን አጠቃላይ የክርስትናን እምነት ማዕከል ያደረገና ከሞት ወደ ዘላለማዊ የሕይወት አቅጣጫ ያሻገረም ጉዳይ ነው። ታላቅነቱም በጊዜ የተገደበ ስላልሆነ (ህያው በመሆኑ) እና ራሱ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሰጠው ወይም ያደረገው ምህረት በመሆኑ ታላቅ አሰኝቶታል።
የሰው ልጅ ይህ ታላቅ መዳን ለምን አስፈለገው? ያሉ እንደሆነ:- መፅሐፍ ቅዱስ ሲናገር ሰው ሁሉ ኋጢአተኛ እንደሆነ ነው። ኋጢአተኝነቱም የመጣው በአዳም ኋጢአተኛ ማንነት ስለተወለድን እንደ ሆነ ሮሜ 5፥12 ይናገራል። ስለሆነም አዳም እግዚአብሔር ያዘዘውን ትዕዛዝ በተላለፈ ጊዜ ኋጢአት ወደ ዓለም ከመግባቱም ባሻገር ባለመታዘዝ ጠንቅ እግዚአብሔር የፈረደው የሞት ፍርድ ለሰው ሁሉ ሊደርስ ችሏል። እስኪ ሰለ ሰው ኋጢአተኝነት መፅሐፍ ቅዱስ ምን ይላል የሚለውን በጥቂቱ ተመልከቱ:-
ብሉይ (አሮጌው) ኪዳን
=}} "ሁላችን እንደ ርኩስ ሰው ሆነናል፥ ጽድቃችንም ሁሉ እንደ መርገም ጨርቅ ነው፤ ሁላችንም እንደ ቅጠል ረግፈናል፥ በደላችንም እንደ ነፋስ ወስዶናል። " (ኢሳ 64፥6)
=}} "ሁሉ ዐመፁ በአንድነትም ረከሱ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ የለም። " (መዝ 14፥3)
አዲስ ኪዳን
=}} "ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል " (ሮሜ 3፥23)
=}} '' ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፤ አስተዋይም የለም፤ እግዚአብሔርንም የሚፈልግ የለም፤ ሁሉ ተሳስተዋል፥ (ሮሜ 3፥11-12)
በአንድነትም የማይጠቅሙ ሆነዋል፤ ቸርነት የሚያደርግ የለም፥ አንድ ስንኳ የለም። ''
በነዚህ የመፅሐፍ ቅዱስ ንባቦች መሰረት የሰው ዘር በሙሉ በኋጢአት ውስጥ እንደሆነና በራሱ ኋጢአት ከሚያስከትለው የሞት ፍርድ (ሮሜ 6፥23 የኋጢአት ደሞዝ ሞት ነው) ሊያድን ባለመቻሉ የእግዚአብሔር ማዳን አስፈልጎታል። የሰው ዘር በአጠቃላይ ከፀሐይ መውጫ እስከ መጥለቂያው ያለን ሰው ሁሉ ከነበረበት መሰረታዊ ችግር እንዲድን በምህረቱ ብዛት ባለጠጋ የሆነው አባታችን እግዚአብሔር አንድ የመዳን መንገድ አዘጋጀ እርሱም አንድያ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። (ዮሐ 14፥6)
ኢየሱስ
ከስሙ ትርጉም ብንነሳ ኢየሱስ ማለት ሕዝቡን ከኋጢአታቸው የሚያድን ማለት ነው (ማቴ 1፥23)። ኢየሱስ የአባቱን ፈቃድ በመታዘዝ እስከ ሞት ድረስ ዋጋ በመክፈል የሰውን ልጅ ከነበረበት ኩነኔ ነፃ አድርጎአል። እስኪ እነዚህ የመፅሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች አንብቡ
" የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአለና"
(ሉቃ19፥10) " በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ። እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ" (ዮሐ 1፥29) " ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው " (1ኛጢሞ1፥15) " ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ " (1ኛ ጴጥ 2፥24)
እነዚህ ጥቅሶች ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር በሙሉ የማዳን ዓላማ ይዞ ከሰማይ እንደመጣ ያሳያሉ። በመሆኑም እርሱ ኋጢአት ስለሌለበት ስለእኛ መሞትና ከኋጢአታችንም ማዳን ተችሎታል። ይህን የማዳን ስራ በሰማይም ሆነ በምድር ከጌታችን ከመድሃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር የተቻለውም የሚቻለውም የለም። የእግዚአብሔር ቃል በሐዋርያት ሥራ 4: 12 ተፅፎ እንደምናነበው "፤ መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና። "
ይህ መዳን እግዚአብሔር አባታችን እንደባለጠግነቱ መጠን እንዲያው በፀጋው ያደለን ነፃ ስጦታችን ነው። በመስራት ያላይደለ በመቀበል የሚገኝ መዳን። ለዚህም አሁንም መፅሐፍ ቅዱሳችን ያረጋግጥልናል። ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ፥ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም። (ኤፌ 2፥4-9)
እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፥ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለ ነበረው ሥራ አይደለም፤ ያን መንፈስም፥ በጸጋው ጸድቀን በዘላለም ሕይወት ተስፋ ወራሾች እንድንሆን፥ በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ላይ አትርፎ አፈሰሰው። (ቲቶ 3፥4-7)
ኢየሱስ ከእያንዳንዳችን የጎደለብንን የእግዚአብሔር ክብር ደግሞም ከኋጢአታችን የተነሳ ተላልፎብን ከነበረው ዘላለማዊ የሞት ፍርድ (ሮሜ 6፥23) ውስጥ ለሚኖር ሁሉ ይህን የኢየሱስ ክርስቶስ ብቸኛ አዳኝነት መስማት ታላቅ የምስራች ነው።
ይህን የምታነቡ ወንድምና እህቶች የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ያደረገልንን ይህን ታላቅ መዳን ቸል ብንል ከሞት ፍርድ እንዴት እናመልጣለን? አይምሰላችሁ እንዴትም አናመልጥም። ይልቅስ ሐዋርያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በፃፈው መልእከቱ ላይ " እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፥ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል፥ ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፥ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ " (ኤፌ 1፥13) እንዳለው ኢየሱስን የሕይወታችን መድሃኒት በማድረግና እርሱን በማመን በሚገኝ ቅድስና ቀሪውን ዘመናችሁን በእርሱ ለመኖር አሁኑኑ ይወስኑ።
ይህንንም ለማድረግ ቀጠሮ አትያዙ ለመልካም ነገር ቀጠሮ አያስፈልገውምና አሁኑኑ ወስኑ። መፅሐፍ ቅዱስ '' እነሆ የተወደደ ሰዓት አሁን ነው እነሆ የመዳንም ቀን አሁን ነው '' ይላልና (2ኛ ቆሮ 6፥2) " በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና። " (ዮሐ 3፥16) ተብሎም እንደተፃፈ እግዚአብሔር ያዘጋጀውን ዘላለማዊ መፍትሄ ልጁን ኢየሱስን በማመንና ራስህን ወይም ራስሽን በንሰሐ መንፈስ በክርስቶስ ደም በመታጠብ ብቻ ወደሚገኝ ቅድስና በመምጣት ክፉ ከሆነው ከዚህ ዓለም ድነው የዘላለም ሕይወት ያገኙ ዘንድ በፀሎት መንፈስ ይህ ተፃፈ።
Sunday, 15 September 2019
ልዩነት
ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ እንዲሁ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና።
1ኛ ቆሮ 15፥22
የሰው ልጅ አስቀድሞ ሲፈጠር ዘላለማዊነትን ከእግዚአብሔር ተሰጥቶት ነበረ፡፡ ሰው ደካማ ሆኖ በመገኘቱ የፈጣሪውን ትዕዛዝ ባለመጠበቁና በማሳዘኑ የተነሳ ዘላለማዊ መሆኑን አስቋርጦ ነበረ፡፡ ቋሚ የነበረው በገዛ ስራውና እምነት በማጉደሉ በሞት ቅጣት የመኖሪያ ገደብ መጣበት፡፡
ታዲያ የሰው ልጅ ምንም እንኳ በገዛ ፈቃዱ ወዶና ፈቅዶ አምላኩን ቢበድልም እግዚአብሔር ግን በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ (ኤፌ 2÷4) የሰውን ልጅ ከፍጥረቱ በሙሉ አክብሮና አልቆ በራሱ መልክና አምሳል ስለፈጠረው የአሳቹ የዲያብሎስ ተገዥ ሆኖ እንዲቀር አልወደደምና ለትዕዛዝ ተላላፊው አዳም የመዳን ተስፋ ተሰጠው እርሱም የዓለምን ኋጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ (ዮሐ 1÷29) የናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።
እግዚአብሔር እኛን ሲፈጥረን እንዳችን ከአንዳችን እንዳንመሳሰል አድርጎ ነው፡፡ ሁላችንም የየራሳችን መልክና ገጽታ እንዲኖረን አድርጎ ነው የፈጠረን፡፡ ይህ ማለት ግን እግዚአብሔር ፍትሃዊ አይደለም አያስብልም ምክንያቱም የሁላችንንም ልዩነት አንድ አካል ወደምንሆንበት ወደ ልጁ ህብረት ጠርቶናልና (1ኛ ቆሮ 1÷9) ለዚህም አንድያ ልጁን እስከማይራራ ድረስ ለሞት አሳልፎ ሰቷልና፡፡ የሰው ልጅም ትልቁ ድል በጌታ የመሆኑ ጉዳይ የሆነውም ለዚህ ነው፡፡ የቱንም ያህል የአሰተሳሰብም ሆነ߹ ሌላ ልዩነት በመካከላችን ቢኖርም በዚህ ልዩነት ውስጥ ተስማምተን በፍቅር እንድንኖር ቃሉ ይነግረናል (ሮሜ 12÷18)፡፡ ፍቅር ነውና ያዳነን፡፡
እኛ ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ ከሌሎች ተሽለን የምንታይበትን ነገር እንፈልጋለን፡፡ ሰዎች በአትኩሮት እንዲመለከቱን ከመፈለጋችን የተነሳ እይታ ውስጥ ለመግባት ብዙ እንጥራለን ነገር ግን እግዚአብሔር እንደሚያየው ሰው አንኖርም፡፡ በሰው ፊት እንጂ በእርሱ ፊት ለመኖር አናስብም፡፡ ለምድራዊ ሕይወት ብዙ እንለፋለን የሰማያዊውን (ዘላለማዊውን) ግን በዳተኝነት እንኖራለን፡፡ ለስጋዊ ሕይወት የምንደክመውን ያህል ለመንፈሳዊ ሕይወት እምብዛም ነን፡፡ ለዚህ ነው እግዚአብሔር የሰው ልጅ የልቡ ሀሳብና ምኞት ሁልጊዜ ፈጽሞ ክፉ እንደሆነ አየ ተብሎ የተጻፈው ዘፍ 6÷5፡፡
የሰው ልጅ ውድቀት በአዳም አለመታዘዝ እንደመጣና (ዘፍ 3÷17 ) ደሞዝ የሆነውን ሞት ለትውልዱም ጭምር ደረሰበት ሮሜ 5÷12፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ገዢ እንደመሆኑ በቃሉ በኩል እንድናደርገውና ደግሞ እንድንታቀብ የሚከለክል ትዕዛዝ አለው፡፡ ፊተኛው አዳም የተሰጠውን ትዕዛዝ በመተላለፉ በኋጢአት ሲወድቅና ሲራቆት እናነባለን። ነገር ግን ኋለኛው አዳም (ጌታ ኢየሱስ) በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረዶ ለሞትም ይኽውም የመስቀል ሞት የታዘዘ ሆነ (ፊልጵ 2÷8)፡፡
ፊተኛው አዳም በማጥፋቱ ራቁቱን ሲሆን (ዘፍ 2÷25) ኋለኛው ግን ሁላችንን ስለ ማጽደቅ ያለ ኋጢአቱ በቀራንዮ አደባባይ በመስቀል ላይ እርቃኑን ሆነ (ሉቃ 23÷34)፡፡
ፊተኛው አዳም ባለመታመኑ በእርሱ በኩል ኋጢአት በሰው ልጅ ላይ በሙሉ ነገሰ ነገር ግን ቅዱስና ጻድቅ ያለ ተንኮልና ነውር በንጽህና የኖረው ከኋጢአተኞችም የተለየ ኋለኛው አዳም በመስቀል ላይ በሰራው ስራ ነውራችንን ሸፈነ፡፡ ፊተኛው አዳም የስራውን ደሞዝ ወስዶ ለትውልዱም የክፋት ስራውን አጋራ ኋለኛው አዳም ግን ስለ በደላችን ሞቶ ስለ ጽድቃችን ከሙታን ተነሳ፡፡
በፊተኛው አዳም የሁላችንም እጣ ፈንታ ሞት ሲሆን እንደ እግዚአብሔር ያለ ይቅር ባይ የለምና በልጁ በኢየሱስ በኩል ያጣነውን የዘላለም ሕይወት መስጠት ነው (ሮሜ 6÷23)፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችንም ይህን በአጽንሆት ይነግረናል በፊተኛው አዳም ምክንያት እግዚአብሔር በሞት ሲቀጣን ነገር ግን በኋለኛው አዳም የዘላለም ሕይወት ሰጠን፡፡ እውተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን የላክኽውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላለም ሕይወት ናት (ዮሐ 17÷3)፡፡
ውድ እንባቢያን ከሰው የምንጠብቀው አንዳች ነገር እንዳይኖር አርጎ ጌታ ኢየሱስ ጽድቅን አድርጎልናል፡፡ ከእኛ የሚጠበቀው በእግዚአብሔር ፍቃድ ላይ መመስረት ብቻ ነው እርሱም እርሱ በላከው በልጁና በሰራው ስራ ማመን ነው፡፡ ይህን መቀበል ላመነ ሰው ቀላል ነው ነገር ግን እንዴት የዚህን ያህል ይቀላል በማለት ብዙዎች ለመቀበል ተቸግረዋል፡፡ በፊተኛው አዳም የመጣውን ኩነኔ ያለማቅማማት ተቀብለው ሲኖሩ በሚበልጥ የረዳንንና ሌላ ስራ ሳያስፈልግ ዘላለም በሚያድን የኪዳን ደም የገዛንን የኢየሱስን የማዳን ስራ ግን አይቀበሉም፡፡
ቅዱስ ቃሉ በተደጋጋሚ ኢየሱስ የዘላለም ሕይወት እንደሆነ ይነግረናል ከዚህ የሚበልጥ ነገር ከየት ይምጣ?፡ ግልጽና ጥርጥር በማያስነሳ መልኩ እንዲህ ይላል እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፡፡ (ዮሐ 6÷47) የእግዚአብሔር ቃል ሊነግረን በፈለገው መጠን በቃሉ እንድናምን የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የእግዚአብሔር አብ ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ህብረት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን።
Thursday, 12 September 2019
ከየቤታችሁ አንፃር
ነህምያ የፈረሰውን የእስራኤልን ቅጥር ሲያድስ ከፈረሱት በሮች ውስጥ የበጉ በር ተብሎ ከሚጠራው እንደ ጀመረ መፅሐፍ ቅዱሳችን ይናገራል (መፅሐፈ ነህምያ 3፥1)። በጣም የሚደንቀው ግን የእስራኤል ቅጥር ማደስ ያለቀውም በበጉ በር ነው(መፅሐፈ ነህምያ 3፥32) ። በበጉ በር ተጀምሮ በበጉ በር ያለቀ ስራ ለእኛ ለክርስቲያኖች ትልቅ መልእክት አለው። በሕይወታችን እግዚአብሔር ዘመን ሲጨምርልን በክርስቶስ ኢየሱስ ፀጋ ተቀብለን ደግሞም በእርሱ ላይ ባለን እምነት በመፅናት መደምደም እንዳለብን ይነግረናል።
እኔን እጅግ የሚገርመኝ አንድ ነገር አለ። ነህምያ የፈረሰውን ቅጥር እንዲሰራ ከተጠቀመባቸው መንገዶች አንዱ ከየቤታችው አንፃር የነበሩትን የፈረሱትን ቅጥር ወይም በር ማደስ ነበር (መፅሐፈ ነህምያ 3፥28)። ሰው ከፊቱ የተደቀነበትን ችግር መፍታት ከቻለ የእርሱ ችግር ሌላ ሰው ጋር ጉዳት እንዳይደርስ ያደርጋል። በጨረስነው ዓመት በአእምሮዬ የሚመላለስ አቋም አለ። " የድርሻህን ተወጣ " (Play Your Part) የሚል።
ሁሉም ክርስቲያን በአገልግሎት የድርሻውን ቢወጣ ምን ያህል ለውጥ ሊያመጣ እንደሚችል ሳስብ እደነቃለው። አንዱ ከሌላው ሳይጠብቅ በራሱ ማድረግ ያለበትን ቢያደርግ ችግር የምንለውን ነገር በቀላሉ ማለፍ እንችላለን። ከአገልግሎት አንፃር ክርስቲያን የሚሞተው ከሰው የጠበቀ ቀን ነው የሚል ፅሁፍ ያነበብኩት ይህን ለማለት የፈለገ ይመስለኛል።
በዚህ ምድሪቱን በከደነው በጌታ ኢየሱስ ፀጋ የተቀበልነው 2012 ዓመተ ምህረት ጌታን በታማኝነት በማገልገል በየአንፃራችን ያለውን ድርሻችንን የምንወጣበት ዓመት እንዲሆንልንና በእርሱ ላይ ባለን እምነት እንድንፀና ፀጋው ይርዳን። ከሰው የምንጠብቅበት ሳይሆን የድርሻችንን የምንወጣበት ደግሞም ከመገልገል አልፈን የምናገለግልበትና የምንዘረጋበት ዓመት ይሁንልን።
እስራኤላዊያን በነህምያ አስተባባሪነት እያንዳንዳቸው በቤታቸው አንፃር ያለውን ቅጥር እንዳደሱ፥ እያንዳንዱም በቅጥሩ ሥራላይ ድርሻ እንዳላቸው ሁሉ ዛሬም በአዲስ ኪዳን የምንገኝ አማኞች ሁላችን ደግሞም የክርስቶስ አካልብልቶች እንደመሆናችን መጠን በ1ኛ ቆሮንጦስ በምዕራፍ 12 በቁጥር 14 - 31 ላይ እንደተገለፀው ሁላችንም በአካሉ ውስጥ እኛ ብቻ ልንወጣው ወይም ልናደርገው የተገባ ኃላፊነትና ሥራአለን። የማያስፈልግ የአካል ክፍል እንደሌለ ሁሉ የማያስፈልግ (ሥራ የሌለው) ክርስቲያን በእግዚአብሔር መንግስት ውስጥየለም። እያንዳንዳችን በአንፃራችን ያለውን የእግዚአብሔር ሥራ በትጋት እየሰራን የምንኖርበት ዘመን እንዲሆን እርሱ ይርዳን።
እንደ ነህምያበቅንዓት፥ በሙሉ መሰጠትና ቁርጠኝነት በክርስቶስ የተፈጠርንለትን መልካሙን ሥራ ለማድረግ እኛም ፈቃዳችንን ለፈቃዱበማስገዛት፥ ስለ በጎ ፈቃዱ መፈለግንም፥ ማድረግንም በእኛ የሚሰራ አምላክ በእኛ የጀመረውን መልካም ሥራእርሱ ራሱ ይፈፅመዋልና እርሱ ላይ በመደገፍ ማገልገል ይሁንልን።
የተወደደው ዓመታችን በኢየሱስ ስም ይባረከ።
እኔን እጅግ የሚገርመኝ አንድ ነገር አለ። ነህምያ የፈረሰውን ቅጥር እንዲሰራ ከተጠቀመባቸው መንገዶች አንዱ ከየቤታችው አንፃር የነበሩትን የፈረሱትን ቅጥር ወይም በር ማደስ ነበር (መፅሐፈ ነህምያ 3፥28)። ሰው ከፊቱ የተደቀነበትን ችግር መፍታት ከቻለ የእርሱ ችግር ሌላ ሰው ጋር ጉዳት እንዳይደርስ ያደርጋል። በጨረስነው ዓመት በአእምሮዬ የሚመላለስ አቋም አለ። " የድርሻህን ተወጣ " (Play Your Part) የሚል።
ሁሉም ክርስቲያን በአገልግሎት የድርሻውን ቢወጣ ምን ያህል ለውጥ ሊያመጣ እንደሚችል ሳስብ እደነቃለው። አንዱ ከሌላው ሳይጠብቅ በራሱ ማድረግ ያለበትን ቢያደርግ ችግር የምንለውን ነገር በቀላሉ ማለፍ እንችላለን። ከአገልግሎት አንፃር ክርስቲያን የሚሞተው ከሰው የጠበቀ ቀን ነው የሚል ፅሁፍ ያነበብኩት ይህን ለማለት የፈለገ ይመስለኛል።
በዚህ ምድሪቱን በከደነው በጌታ ኢየሱስ ፀጋ የተቀበልነው 2012 ዓመተ ምህረት ጌታን በታማኝነት በማገልገል በየአንፃራችን ያለውን ድርሻችንን የምንወጣበት ዓመት እንዲሆንልንና በእርሱ ላይ ባለን እምነት እንድንፀና ፀጋው ይርዳን። ከሰው የምንጠብቅበት ሳይሆን የድርሻችንን የምንወጣበት ደግሞም ከመገልገል አልፈን የምናገለግልበትና የምንዘረጋበት ዓመት ይሁንልን።
እስራኤላዊያን በነህምያ አስተባባሪነት እያንዳንዳቸው በቤታቸው አንፃር ያለውን ቅጥር እንዳደሱ፥ እያንዳንዱም በቅጥሩ ሥራላይ ድርሻ እንዳላቸው ሁሉ ዛሬም በአዲስ ኪዳን የምንገኝ አማኞች ሁላችን ደግሞም የክርስቶስ አካልብልቶች እንደመሆናችን መጠን በ1ኛ ቆሮንጦስ በምዕራፍ 12 በቁጥር 14 - 31 ላይ እንደተገለፀው ሁላችንም በአካሉ ውስጥ እኛ ብቻ ልንወጣው ወይም ልናደርገው የተገባ ኃላፊነትና ሥራአለን። የማያስፈልግ የአካል ክፍል እንደሌለ ሁሉ የማያስፈልግ (ሥራ የሌለው) ክርስቲያን በእግዚአብሔር መንግስት ውስጥየለም። እያንዳንዳችን በአንፃራችን ያለውን የእግዚአብሔር ሥራ በትጋት እየሰራን የምንኖርበት ዘመን እንዲሆን እርሱ ይርዳን።
እንደ ነህምያበቅንዓት፥ በሙሉ መሰጠትና ቁርጠኝነት በክርስቶስ የተፈጠርንለትን መልካሙን ሥራ ለማድረግ እኛም ፈቃዳችንን ለፈቃዱበማስገዛት፥ ስለ በጎ ፈቃዱ መፈለግንም፥ ማድረግንም በእኛ የሚሰራ አምላክ በእኛ የጀመረውን መልካም ሥራእርሱ ራሱ ይፈፅመዋልና እርሱ ላይ በመደገፍ ማገልገል ይሁንልን።
የተወደደው ዓመታችን በኢየሱስ ስም ይባረከ።
Subscribe to:
Posts (Atom)