Monday, 6 April 2020

መጠንቀቅ መፍራት አይደለም


" ሕዝቤ ሆይ፥ ና ወደ ቤትህም ግባ፥ ደጅህን በኋላህ ዝጋ ቍጣ እስኪያልፍ ድረስ ጥቂት ጊዜ ተሸሸግ። " (ኢሳ 26፥20)

ሰሞኑን የሁሉም ሰው ጸሎትና ምልጃ ዓለምን እያዳረሰ ያለውን የኮሮና በሽታ መፍትሄ ከእግአብሔር ይመጣ ዘንድ ነው። በሌላ ጎን ደግሞ የዓለም ጠቢባን፣ ሳይንቲስቶች፣ ተመራማሪዎች፣ ዶክተሮች ኃያላን ተብለው የሚጠሩ ሀገራት በሙሉ በጭንቅ መፍትሄ ፍለጋ ቫይረሱን እንዳይዛመትና እንዳይሰራጭ ለማድረግ ብሎም ማጥፋት የሚቻልበትን መንገድ ለማግኘት ያለ እንቅልፍ ይዳክራሉ ግን እስካሁን ምንም አላገኙም።

እኔ የማመልከው ጌታ ኢየሱስ ግን ቫይረሱ ለመስፉፉት፣ ለመባዛት እንዲሁም ለመግደል የሚመቸውንም ነገሮች ቢሆን ተጠቅሞ ሊያስወግደው እንደሚችል አምናለው። ያለ እርሱ ይህን ጊዜ ማለፍ አይቻልም።

የዚህ በሽታ መስፋፋት ከተሰማበት ጊዜ ጀምሮ በግልና በተቋም እንዲሁም በመንግስትና በዓለም አቀፍ ደረጃ ሳይቀር ጊዜአዊ የተባሉትን የመከላከያ ዘዴዎች እየተከናወኑ ይገኛል። በመሆኑም የሚደረጉትን ጥንቃቄዎች እንደፍራቻ የተመለከቱት ሰዎች ገጥመውኛል በተለይ ክርስቲያኖች።

መፍራትና መጠንቀቅ እጅግ መቀላቀል የሌለባቸው የተለያዩ ሀሳቦች ናቸው። ሁለቱንም ሀሳቦች በልቶ ማየት ያስፈልጋል። መጽሐፍ ሲናገር "፤ ጥንቃቄ ይጠብቅሃል፥ ማስተዋልም ይጋርድሃል፥ " (ምሳ 2፥11) ይላል ይህን ቃል የሚያምን ሁሉ በሕይወት ዘመኑ ይጠነቀቃል በማስተዋል ይራመዳል ነገር ግን የመኖሩ ህልውና በመጠንቀቁና በማስተዋሉ እንዳልሆነ በመረዳት ጭምር ማለት ነው። የሚገርመው ነገር እንደዛም ሆኖ መጠንቀቅ ግድ ነው። " በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን፥ በራስህም ማስተዋል አትደገፍ " (ምሳ 3፥5) ተብሎም እንደተፃፈ።

ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ ሲናገር  " ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ። " (ማቴ 10፥28) እንዳለው አማኝ ማንን መፍራት እንዳለበት የተረዳ ይመስለኛል። አሁን እየተደረጉ ያሉት መከላከያዎች ቫይረሱን ፍራቻ ሳይሆን ከጥንቃቄ አንፃር ብቻ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል። በመንግስትም ሆነ በጤና ባለሙያዎች የሚነገረውን መከላከያ (መታጠብ፣ መራራቅ ፣ መሸፈን፣ መቀመጥ/ቤት)  መተግበር የክርስቲያን ግዴትም ጭምር ነው። ጊዜውን የሚዋጅና ለሌላውም ምሳሌ የሚሆን ልበ ሙሉ ክርስቲያን ሆኖ መገኘት ያሻል።

ያለዚያማ ..... ያለዚያማ........ " እምነትና በጎ ሕሊና ይኑርህ፥ አንዳንዶች ሕሊናን ጥለው፥ መርከብ አለ መሪ እንደሚጠፋ፥ በእምነት ነገር ጠፍተዋልና " (1ኛ ጢሞ 1፥19) እንዳይሆን ነገሩ።

እርሱ አሰራሩ ብዙ የሆነ ጌታ ባሻው መንገድ ይጠብቅሃል ካሻውም ደግሞ በአንተ መጠንቀቅ ውስጥ ጣልቃ ገብቶ ይጋርድሃል። ካስፈለገም ምንም ጥንቃቄ ባላረክበትም ሁኔታ ይጠብቅሃል። ስለሆነም ያንተ ድርሻ በጥንቃቄ መሄድ ቀሪውን ለሠሪው መተው ይህ የበዛ ማስተዋል ነውና። ደግሞም መጠንቀቅ ለራስ ብቻ ሳይሆን ለሌላውም ነውና የሚበረታታ ጉዳይ ነው።

አዎ መጠንቀቅ መፍራት አይደለምና የድርሻችንን በመወጣት በጌታ ሁሉን አድራጊነት ሁላችንም ማለፍ ይሁንልን። አሜን

ምሽጌን በደም ገንብተህ
ማማዬን በፍቅር ሰርተህ
አንግቼ ያንተን ጦር ዕቃ
ኃይልህን ነፍሴ ሰንቃ
አሸነፍኩ ሆነህ ደጀኔ
ተጋድለህ ድልነሳሁ እኔ
ተሰዷል የሚያሳድደኝ
በትርና ምርኩዝ ሆነኸኝ
ማይገፉህ ፅኑ ድንበሬ
መኖርያ እናት ሀገሬ
አላውቅም ባንተ ድርድር
መውደዴ ያልፋል መቃብር

ደኅና ነው!!!



" መልካሙን የምሥራች የሚያወሩ እግሮቻቸው እንዴት ያማሩ ናቸው '' (ሮሜ 10፥15)

መቼም በዚህ ጊዜ መልካም ወሬ መስማት የማይፈልግ ይኖራል ብዬ አላስብም። የሰው ሁሉ ወይይት፣ የዜና አውታሩ ሰበር ዜና፣ የማህበራዊ ሚዲያ ዘገባ፣ የቴሌቪዥኖች ዳሰሳ የራዲዮኖች ድምፅ፣ የባለሙያዎች ምክር፣ የመንግስት መግለጫ .....ወዘተ  ስለ ሰሞንኛው ኮሮና ቫይረስ ነው። በሁሉም አቅጣጭ ማለት በሚቻል መልኩ የሚነገሩት አዳዲስ ክስተቶች ሁሉ የሚያሳዩት ነገሩ እየባሰ እንደሆነም ጭምር ነው።

መልካም ነገር መስማት የተጠማ ብዙ ጆሮዎች ስለመኖራቸው ማስረጃ ማቅረብ የሚጠይቅ ጉዳይ አይደለም። ስንት ታማሚ ጨመረ፣ ምን ያህል ሰው ሞተ፣ የት ሀገር ደረሰ፣ ብሎ የሚጠይቅ እንጂ ስንቱ አገገመ የሚል እምብዛም ነው።

ታዲያ በዚህ ጊዜ የበረታ የተጨነቁትን ማበርታት፣ መልካም ወሬ በሌለበት ሁኔታ ውስጥ እንኳ ብንሆን ሰውን የሚያፅናና ቃላትን መጠቀም ያስፈልጋል። በተለይ ክርስቲያኖች ሁሉን ያደርግ ዘንድ ቻይ፤ ሀሳቡም ይከለከል ዘንድ የማይቻል አምላክ ዛሬ በብርታት በላይ በራማ በዙፋኑ ከዚህ ነገር በእርግጥ ያወጣናል ብለን ለምድሪቱ መፅናናት ጉልበት መሆን አለብን።

ያቺ ልጇ ሞቶባት አልጋ ላይ አስተኝታው የቤቱን በር ዘግታበት በመንገድ ላይ ሁለት ጊዜ ምን እንደሆነች ስትጠየቅ '' ደኀና ነው '' እንዳለችው ሱነማዊቷ ሴት (መጽሐፈ ነገሥት ካልዕ 4፥17-26) እኛም '' የደኀና ነው '' ወሬ መናገር አለብን። እግዚአብሔር አይተወንም ክንዱን ያነሳል ዓለምን ያስጨነቀ ለእርሱ ምንም ነው ማለት ይጠበቅብናል።

በያለንበት ከፀሎትም ባሻገር በዘንዳችን ያሉትን እናበርታ እግዚአብሔር ይህን ጊዜ ያለ ሞት ሀገራችንን በኢየሱስ ስም ያሳልፍልን።

ለሰው የማይቻል
ለእርሱ ይቻላል
ደኀና ይሆናል
በነበር ይቀራል
ይህም ጊዜ ያልፋል።
እያልን እንመስክር
እስኪሰማን ሀገር
ተስፋው እስኪጨምር
ክርስቲያን ተናገር
ይሰራል እግዚአብሔር።