Saturday, 29 May 2021

በፍጹም ልብህ

 

አንዳንድ ጊዜ ብዙ ከመጠንቀቅ እና ሕይወታችንን በማስተዋል ከመምራታችን የተነሳ ስኬታማ ወይም ውጤታማ ኑሮ እንዳለን የምንቆጥር ልንኖር እንችላለን። በእርግጥ መጠንቀቅም ሆነ ማስተዋል አስፈላጊ ነገሮች ናቸው። '' ጥንቃቄ ይጠብቅሃል፥ ማስተዋልም ይጋርድሃል '' (ምሳሌ 2፥11) እንደሚል መፅሐፍ። ነገር ግን ለደረስንበት ደረጃ ራሳችንን ድጋፍ የምናደርግ ከሆነ ተሳስተናል። 

እኔ እንደገባኝ በራስ መደገፍን የሚያክል አደገኛና ከንቱ ነገር ያለ አይመስለኝም። የቱንም ያህል ብዙ ነገሮችን ያወቅንና አስተዋዮች ብንመስልም የእኛ ማስተዋል ለመደገፍ የሚያበቃ አይደለም። የእኛ ማስተዋል ከሸንበቆነት አይበልጥም ቆመናል ስንል ወድቀን እንገኛለን። 

እስኪ ስንቶቻችን ነን ገና ያልተፈጠን ነገር ሊፈጠር ይችላል ብለን ፍርሃት በፈጠረው በገዛ ፈቃዳችን ተመስርተን ነገሮችን እንዳይሆኑ ያደረግን/የተከላከልን የሚመስለን? ለራሳችን ልክ የሆንባቸው ጉዳዮች ላይ ሰው አለማሳዘናችን እርግጠኞች ነን ወይ? ደግሞም ማስተዋል አለኝ ተብሎ ክርስቲያን ብልጣብልጥ እንዲሆን ተፈቅዶለታል ወይ? ራሳችንን እንጠይቅ

እውነት እውነት እላችኃለው የእኛ ማስተዋል ከእግዚአብሔር ሞኝነት አይበልጥም። '' ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና፥ የእግዚአብሔርም ድካም ከሰው ይልቅ ይበረታልና። '' (1ኛ ቆሮ 1፥25)

እኛ ችሎታችንና አቅማችን እጅግ ውሱን ስለሆነ ያለ እግዚአብሔር እርዳታ በማስተዋልና በጥንቃቄ እንኳ ቢሆን አንዳች ልናደርግ አንችልምና ለደረስንበት ማንኛውም ደረጃ ክብሩን ለእርሱ እንስጥ። እግዚአብሔር አደረገልን ማለትን እናብዛ በማንኛውም ሰበብ ክብሩን ለሌላ አንስጥ። 

እንዴት እንደሚሠራና ነገሮችን እንደሚያቀናጅ ዝርዝሩንና ስሌቱን ወይም ቀመሩን አናውቅምና ለአሠራሩ ፍፁም እንድንመች ፍፁም እንመነው ፍፁም ይሰራብናል።

ሁሉን ቻይነቱና ሀሳቡም ይከለከል ዘንድ በማይቻል በእርሱ እንደገፍ ባይዋጥልንም የራሳችንን አካሄድ ትተን ፍለጋውን እንከተል! እንዲህ ተብሎ ተጽፏልና '' የነፋስ መንገድ እንዴት እንደ ሆነች፣አጥንትም በእርጉዝ ሆድ እንዴት እንድትዋደድ እንደማታውቅ፣ እንዲሁም ሁሉን የሚሠራውን ሥራ አታውቅም '' (መክብብ 11፡4-5) 

በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን፥ በራስህም ማስተዋል አትደገፍ፤ በመንገድህ ሁሉ እርሱን እወቅ፥ እርሱም ጎዳናህን ያቀናልሃል። በራስህ አስተያየት ጠቢብ አትሁን፤ እግዚአብሔርን ፍራ፥ ከክፋትም ራቅ፤ ይህም ለሥጋህ ፈውስ ይሆንልሃል፥ ለአጥንትህም ጠገን። እግዚአብሔርን ከሀብትህ አክብር፥ ከፍሬህም ሁሉ በኵራት፤ (ምሳ 3፥5-9)

ቸር እንሰንብት !

Tuesday, 4 May 2021

የእኛ ዶሮስ?

መፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉት ሁሉም ነገሮች ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ይጠቅመን ዘንድ ተፅፎልናል የቅዱሳን የሕይወት ታሪክ ጭምር (2ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 3: 16-17)። ነገር ግን ቃሉ ሊነግረን በፈለገው መጠን አንረዳውም። በሕይወት እስካላዋሃድነው ድረስ የቃሉ ጉልበት አይታወቀንም። አንዳንዴ ከታሪክ ባልዘለለ መልኩ እናየዋለን። በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተፃፈው ሁሉ በዓላማና እኛም ልንማርበት ታቅዶ ነው። በዘፈቀደ ያለ ምንም ቃል የለም። 

የጴጥሮስን ዶሮ ብዙ ጊዜ የሚጠቀሰው በፋሲካ ሰሞን ነው ነገር ግን ዛሬም በየአንዳንዱ ዛሬ ዶሮ ይጮሃል። ብዙዎቻችን በጴጥሮስ ላይ ብቻ የጮኧች አርገን እናስባለን። ዶሮዋ ጴጥሮስ ላይ  መጮዋ እኛ ሕይወት ላይ ምን ፋይዳ አመጣ ብለን ካልጠየቅን ስለምን ለትምህርት ተፃፈ ማለት እንችላለን? 

እርግጥ ነው ጴጥሮስ በጊዜው በራሱ ተማምኖ ሌሎች ቢሸሹ እንኳ እኔ ግን አልተውህም ብሎ ቢናገርም ያች ዶሮ እንዳትጮው ማድረግ አልቻለው። ዶሮዋ እስክትጮው ድረስ ጴጥሮስ በራስ ተማምኖ ነበር። አንዴ ካዴ ደግሞም ሁለቴ ያን እንኳ ከነበረበት የራስ መተማመን ሊባንን አልቻለም የሶስተኝው ግን የጌታ ቃል ነውና በእርግጥ ባነነ። ዛሬስ እኛ ከዚህ የምንማረው ምንድነው? 

ያች ዶሮ ጴጥሮስን ወደ ንስሀ አስገሰገሰችው እናም ወዲያው በመፀፀቱና በማንባቱ በደሉ ይቅር ተባለችለት። እኛ ስንት ዓመት በየማለዳው ዶሮ ሲጮው ከነበርንበት በደልና እግዚአብሔር እንደቃሉ አለመታዘዝ ቀስቅሶን ይሆን? ይህን የራሳችን ጉድ የምናውቀው ራሳችን ነን። ስንት ዓመት የዶሮዋን ጪወት ለጴጥሮስ ብቻ አርገን አሰበነው? ዛሬም በበደል ላለ ሰው የዶሮ ጩወት ለጴጥሮስ እንደጮኧችው አይደለምን? ጪወቷን ስንሰማ ለንስሀ ማንቂያ ወይስ ከእንቅልፍ ማንቂያ? 

መስማት ይሁንልን። በራሳችን ወይም በዚህ ዓለም ማስተዋል ሳይሆን በእግዚአብሔር ማስተዋል  እንመላለስ ዘንድ የእርሱ መሉም ፈቃድ ይሁን። አሜን