ብዙዎቻችን '' ምስል ፍቅር ወልዳ '' የሚለውን ስዕል ሉቃስ እንደሳለው ሲነገር እንሰማለን። እንደ ሃይማኖቱን ለሚወድና የቤተክርስቲያን አባቶችን ቃል ከመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በላይ ለሚወስድ የሚረገረውንም ነገር ያለ ጥያቄ ለሚቀበል ማንኛውም ሰው፤ ማርያም ጌታ ኢየሱስን አቅፋ የሚያሳየው ስዕል ደስ ሊያሰኘው ይችላል። ነገር ግን እንደ ባለአእምሮና አስተዋይ ሁሉን በቃሉ እንደሚመረምር ሰው ግን ለምንና እንዴት ያሉ መሰል ጥያቄዎችን መጠየቅና እውነቱን ለማወቅ መጣር አስፈላጊም ተገቢም ነው።
እኔ ከጌታ እናት ማርያም አንዱ የምማረው ነገር '' ይህ እንዴት ይሆናል '' የሚለውን ጥያቄ ነው። " ማርያምም መልአኩን። ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል? አለችው። " (ሉቃ1፥34) እንኳን ሰው ይቅርና መላእክት እያናገረህ ጥያቄ ጠይቆ እውነቱን መረዳት ከእሷ እማራለው። አዎ ይህ መሰረታዊና ዛሬ ለቆምኩበት እውነት ጠይቆ መረዳትንና ቃሉን መመርመር ወሳኝነት አለው። ዝም ብሎ ስለተባለና በዛ በሚባልበት ስፍራ ረጅም እድሜ ከነገሩ ጋር አብሬ መኖሬ የተባለውን ነገር እውነተኛ አያሰኘውም።
ድንግል ማርያም ልጇን ይዛ ተስላለች ብሎ ለሚያምን ሰው ቢያንስ መሰረታዊ ጥያቄዎችን መጠየቅና መረዳት አለበት ብዬ አስባለው። በመጀመሪያ ደረጃ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ተቀረፀ ምስልና ስዕል ምን ይላል? የእግዚአብሔር ሀሳብስ ምንድነው? ብሎ መጠየቅ እጅግ መሰረታዊ ነው በተለይ በአዲስ ኪዳን። የሚገርመው በዛ በአሮጌው ኪዳን እንኳ እግዚአብሔር ይህን ብሏል......
" እኔ እግዚአብሔር ነኝ፤ ስሜ ይህ ነው፤ ክብሬን ለሌላ፥ ምስጋናዬንም ለተቀረጹ ምስሎች አልሰጥም። " (ትንቢተ ኢሳይያስ 42፥8) ልጁን ቤዛ ሊቀካህን አርጎ በሾመበት አዲስ ኪዳን ደግሞ "፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል። " (የዮሐንስ ወንጌል 4፥24) ተብሎ ተፅፏል።
ሲቀጥል ወንጌላዊው ሉቃስን ሰዓሊ አርጎ ማምጣት ስዕሉን መንፈሳዊ ያደርገዋል ወይ? ይህን የምጠይቀው የብዙዎች መከራከሪያ ሉቃስ ስለሳለው ተቀባይነት እንዳለው አድርገው ማመናቸው ነው። አበበም ሳለው ከበደ ስዕሉ ምን ለውጥ አለው?
ቅዱሳት መፃህፍት በእግዚአብሔር መንፈስ ስለመፃፋቸው ማስረጃ ማቅረብ ይቻላል ስዕል ግን ፍፁም የለም ???
ሌላው ሉቃስ ስሎታል የሚባለው ስዕል ኢየሱስ ህፃን እያለ በእናቱ እቅፍ ውስጥ ሆኖ ነው። ለመሆኑ ሉቃስና ኢየሱስ መች ነው የተገናኙት? የተሳለውስ ህፃን ሆኖ ነው ወይስ ካደገ በኃል በምናብ ነው? በጣም ደግሞ የሚገርመው የስዕሉ የአሳሳል ዘይቤ ድንግል ማርያም በምድራዊ በረከት እጅግ የከበረችና የናጠጠች ሐብታምና የቤተመንግስት ንግስት አስመስሎ መሳሉና ኢየሱስን ደግሞ እንደ ፊልም ማሳመሪያ ውብና ቆንጆ አድርጎ መሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ ከነገረን ጋር እጅግ የሚጣላና የማይስማማ ያደርገዋል።
ድንግል ማርያም ጌታን እንዴት እንደወለደችውና በምን ያህል ዋጋ በመክፈል እንዳሳደገችው ለሚያውቅ ሰው በተዋበ አልባስ፣ የወርቅ ፈርጥ ያለበት የሐር ልብስና የወርቅ አክሊል ሲያይ መጠየቅ ያለበት ጉዳይ አለ። መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር መስዋዕት ሲያቀርብ ጠቦት ለማምጣት ገንዘብ ላልበቃው ሰው የሰጠው አማራጭ ርግብ አንዱ ነው (ዘሌ 5፥7)። ድንግል ማርያምን ስሏታል የተባለው ሉቃስ የፃፈው ወንጌል ላይ ግን ያቀረበችውን ስንመለከት ግጭት ይፈጥርብናል።
"፤ እንደ ሙሴም ሕግ የመንጻታቸው ወራት በተፈጸመ ጊዜ፥ በጌታ ሕግ። የእናቱን ማኅፀን የሚከፍት ወንድ ሁሉ ለጌታ የተቀደሰ ይባላል ተብሎ እንደ ተጻፈ በጌታ ፊት ሊያቆሙት፥ በጌታም ሕግ። ሁለት ዋሊያ ወይም ሁለት የርግብ ጫጩቶች እንደ ተባለ፥ መሥዋዕት ሊያቀርቡ ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት። " (የሉቃስ ወንጌል 2: 22-24)
ኢየሱስን ደግሞ ይወደድ ዘንድ ደምግባት እንዳልነበረው (ኢሳ 53) እና የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ (ፊልጵ 2፥7) ተብሎ እንጂ እንደ HOME ALONE ሆሊውድ ፊልም ቆንጅዬ ሲያዩት የሚያሳሳ ድንቡሽቡሽ ልጅ እንዳልሆነ መረዳት እንችላለን። ይህስ ጥያቄ መመለስ የለበትም?
ይህ ጉዳይ ሲነሳ እጅግ የሚደንቀኝ ነገር ደግሞ ሳለው የተባለው ሉቃስ ራሱ በፃፈው በሐዋርያት ስራ ላይ የፃፈው ትዝ ሲለኝ ነው። በነገራችን ላይ መጽሐፍ ቅዱስ ሉቃስ ባለመድሂት እንጂ ሰዓሊ እንደሆነ ምንም አልተናገረም። " የተወደደው ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ " (ወደ ቆላስይስ ሰዎች 4፥14)። ምን እንዳለ ታውቃላችሁ?
" እንግዲህ የእግዚአብሔር ዘመዶች ከሆንን፥ አምላክ በሰው ብልሃትና አሳብ የተቀረጸውን ወርቅ ወይም ብር ወይም ድንጋይ እንዲመስል እናስብ ዘንድ አይገባንም። " (የሐዋርያት ሥራ 17፥29)
እንዲህ ያለ ወንጌላዊ ከተናገረው ቃል በተቃራኒ ጊዜውን በእርድና በበርበሬ ቀለም ያጠፋል ብላችሁ ታምናላችሁ? አይመሰለኝም እንደው ነገሩን ለጥጣችሁ አላሰባችሁበት እንጂ ማሰቡንስ አታስቡም ነበር።
አንድ የቤተክርስቲያን አባት በንግስ ጊዜ ይህን ምስለ ፍቁር ወልዳ ስዕል የሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያን ይዘው ሲዘምሩ ያዩና ይህ ህፃን እስካሁን በእናቱ እቅፍ ውስጥ ነው እንዴ ያለው? መች ነው የሚወርደው? ብለው ጠየቁ ይባላል። እናንተስ መቼ ከእናቱ እቅፍ ወርዶ በሰውና በእግዚአብሔር ፊት በቁመትና በሞገስ ካደገ በኃላ ስለ በደልና ኃጢአት ራሱን አሳልፎ በመስቀል ላይ ሞቶ ደግሞም እኔኑን ስለማጽደቅ በሶስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ በመነሳት ለዘላለም እኖርበት ዘንድ ስፍራ ሊያዘጋጅል ወደ አባቱ በመሄድ በማያልፍ የሕይወት ኃይል በግርማ ቀኝ አልተቀመጠምን? ብላችሁ የማትጠይቁት?
ማስተዋል ይብዛላችሁ ከተፃፈው እንዳናልፍ ጸጋው ይርዳን አሜን።